"; _gaq.push(['_trackPageview']);(function() { var ga = document.createElement('script'); ga.type = 'text/javascript'; ga.async = true; ga.src = ('https:' == document.location.protocol ? 'https://ssl' : 'http://www') + '.google-analytics.com/ga.js'; var s = document.getElementsByTagName('script')[0]; s.parentNode.insertBefore(ga, s); })();

[አንድ ለቅዳሜ] የአደባባይ ምሑራኑ የት ገቡ?

አንድ የተማረ ሰው ከምንም ተነስቶ ወደ መጨረሻው ደረጃ ለመድረስ የሚያስችለው ውጫዊ ሁኔታ ከጊዜ ጊዜ፣ ከቦታ ቦታ ይለያያል። ይሁንና እጅግ ወሳኙ ግብአት የግለሰቦቹ ውስጣዊና ግላዊ እምነት፣ ፍላጎት እና ግብ ነው። ቀድሞውኑ የምሁራኑ መገለጫ ነባራዊውን/ያለውን እያጸደቁና እያደነደኑ መኖር ሳይሆን ለሰው ልጅ የተሻለ ሕይወት ለማምጣት ያለውን መለወጥ/መረበሽ ነውና ውጫዊ ሁኔታው ከጅምሩ አጋዣቸው እንዲሆን አይጠበቅም። ይህም ሸክሙን ከውጭ ወደ ውስጥ ይመልሰዋል።

የእኛ የሕዝባዊ ምሁራን እነማን ናቸው? በእኔ ዕድሜ (የላይትማንን ደረጃ ልጠቀምና) ወደ ሦስተኛው ደረጃ መድረስ ችለው የነበሩ የአደባባይ ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ብቻ ናቸው። አሁን ደግሞ ጊዜው አጭር ቢሆንም ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ናቸው። የፕሮፌሰር መስፍን ወደ ፓርቲ ፖለቲካ መግባት (በተለይም የቅርብ ጊዜው የውዝግብ ድራማ) የሚያስነሳው ጥያቄ ቢኖርም ሰውየው ከአደባባይ ምሁርነታቸው የወረዱ አይመስለኝም። ምናልባትም አጋጣሚው የአደባባይ ምሁራንን በፓርቲ ፖለቲካ የሚኖራቸውን ተሳትፎ እንድንቃኝ የሚጠይቅ ነው። ነጻነት ባለበት የምእራቡ ዓለም ያሉና የአደባባይ ምሁር (public intellectual) መባል የሚገባቸው ጸሐፊዎች፣ ተናጋሪዎችም አሉ፣ ቁጥራቸው የእድሉን ያህል አይደለም እንጂ።

This post is available in: ኸንግሊስህ

ከሁለት ዓመት በፊት፤ ዝነኛው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ “ስታፍ ላውንጅ”። በወቅቱ ከሥራዬ በተጨማሪ የዩኒቨርሲቲው የድኅረ ምረቃ ተማሪ ስለነበርኩም ጭምር ከግቢው አልጠፋም ነበር። በንባብና በመጻፍ መካከል የቡና እረፍት ለማድረግ ስታፍ ላውንጅ እንደገባሁ በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ ወደ ተቀመጡት መምህራን እንድቀላቀል የተሰጠኝን የግብዣ ምልክት አክብሬ የጨዋታው ተሳታፊ ሆንኩ። ቦታው ዩኒቨርሲቲ በመሆኑ ብቻ የጨዋታው ርእሰ ጉዳይም ይሁን ይዘት የተለየ እንዲሆን መጠበቅ የዋህነት ነው። ትምህርት የቀመሱ ኢትዮጵያውያን የሚያደርጉት የቡና ላይ ጨዋታ በአብዛኛው መሠረታዊ ጠባዩ አይለወጥም። በየመካከል ሳቅ ጣል እየተደረገበት “የሐሳብ በየአይነቱ” ይነሳል፣ ይወድቃል። ሒሳብ ተወራርዶ አስተናጋጁ የቡና ስኒዎችን ሲሰበስብና ታዳሚዎቹ ለመሄድ ሲነሱ ግን አንዱንም ሐሳብ ቢሆን የምር የሚወስደው ሰው እምብዛም አይገኝም።

ጥቂት ዶክተሮች እና ጥቂት ወጣት መምህራን በተገኙባት ጠረጴዛችን ፖለቲካም፣ የኅብረተሰብ ለውጥም ወዘተ “ጨዋታን ጨዋታ እያነሳው” ተዳሰሱ። ተማሪ ብቻ ሳልሆን ጋዜጠኛም ስለሆንኩ ጭምር ሐሳቦቹን ላለመርሳት ስልኬ ላይ አጫጭር ማስታወሻ መውሰድ ነበረብኝ (የቡና ታዳሚዎቼን ማንነት ለመደበቅ ስል ርእሰ ጉዳዮቹንም እዚህ መጥቀስ አልተገባኝም፤ ይልቁንም ለዚህ ጽሑፍ ጭብጥ የሚረዳ አይደለም)።

በመጨረሻ ሁላችንም ወደየጉዳያችን ስናመራ “ሊጻፍባቸው ይችላሉ” ካልኳቸው ሐሳቦች አንዱን ካነሱት መምህር ጋራ በአንድ አቅጣጫ የምንሄድ ነበርን። አጋጣሚውን ካገኘሁ አይቀር በሚል በርእሰ ጉዳዩ ላይ ማንበብና ጋዜጣ ላይ ጥቂት መስመሮች መጻፍ እንደምፈልግ ነገርኳቸው። ምሁሩን ራሳቸውን “ጻፉልን” ብሎ መጠየቅ ቀላሉ ነገር ነበር፤ ሆኖም ከዚህ ቀደም እንዲህ አይነት ጥያቄ ደግሜ እንዳላነሳባቸው የገባሁትን ቃል ማክበር ነበረበኝ። አስገራሚው ነገር “የማነበውን ጠቁሙኝ” ለሚለው ጥያቄ ጭምር የሰጡኝ መልስ ነው። ሰውየው ጉዳዩን ሌሎች ሰዎች ባሉበት ስላነሳነው አሁን ብጽፍበት ለእርሳቸው ጥሩ እንደማይሆን ነገሩኝ። በጉዳዩ ላይ መጻፌንም ለወራት አቆየሁት። ይህ አጋጣሚ የአገራችን ፖለቲካዊ ምኅዳር ለምሁራን ምን ያህል አፋኝ እንደሆነባቸው ያስታውሳል፤ የዚያኑም ያህል ስለምሁሮቻችን ምንነትና ማንነት እንደገና እንዳሰላስል አስገድዶኝ ነበር።

ብዙዎቹ የኢትዮጵያ ምሁራን አደባባይ ወጥቶ መናገርን አጥብቀው ይጠላሉ። አንዳንዶቹ በራሳቸው የትምህርት ዘርፍ ጭምር ባላቸው እውቀት ስልማይተማመኑ እውቀታቸውን እንደ ጥንቆላ ክታብ ሳይገለጥ እንዲኖር የሚፈልጉ ናቸው። አንዳንዶቹ ደግሞ በራሳቸው ጠባብ የጥናት ዘርፍ የተመሰገኑ ቢሆኑም “ፖለቲካን” በተመለከተ ያላቸው አመለካከት በጣም የተዛባ ነው፤ ስለዚህም በሕዝብ አደባባይ ፈጽሞ ባለመገለጥ ከማኅበረሰባቸው የሚደበቁ ናቸው። አንዳነዶቹ ትምህርትን/መማርን እውቀትን እና በዚያም በኩል “እውነትን” የመፈለጊያና የማስፋፊያ መንገድ አድርገው አይመለከቱም፤ ምሁር በመሆንና ሾፌር በመሆን መካከል የሚታያቸው ልዩነት የሚያስገኝላቸው ክብርና ሀብት ብቻ ነው። ስለዚህም አደባባይ የሚወጡት ክብርና ገንዘብ የሚያስገኝላቸው ሆኖ ሲያገኙት እንጂ ስለሌላ የላቀ ዓላማ (መርህ፣ ፍትሕ፣ ነጻነት፣ ሳይንሳዊ እውነት ወዘተ) ሲሉ አይደለም። ጥቂቶቹ በትምህርት ዘርፎቻቸውም ይሁን ከዚያ ውጪ አስተዋጽኦ የማድረግ ማኅበረሳባዊ ሐላፊነት እንዳለባቸው ይረዳሉ፤ ሆኖም አደባባይ ወጥቶ ሕሊናቸውና እውቀታቸው የሚላቸውን በመናገር ማኅበረሰብን ለመቀየር ዋጋ መክፈል አይፈልጉም፣ ወይም ዋጋው ብዙ ሆኖ ይታያቸዋል፣ ወይም ከዚህ ቀደም የከፈሉት ዋጋ (ካለ) በቂ እንደሆነ ያምናሉ። ዝርዝሩ ራሱን የቻለ ጥናት የሚጠይቅ ነው።

ይህ እውነታ አሁን የተፈጠረ አይደለም፤ ቀድሞም የነበረ ነው። በዚህም ምክንያት “ተማሩ” የሚባሉትን ወይም ተማርን የሚሉትን ያህል የአደባባይ ምሁራን (Public Intellectuals) ለማግኘት አልታደልንም። ታዋቂው ጸሐፊ ኤድዋርድ ሴይድ (Representations of the Tntellectual)“ምሁሩ ማን ነው?” የሚለውን የብያኔ ጥያቄ ሲመልስ እንዲህ ይላል፤

“The intellectual is an individual with a specific public role in society that cannot be reduced simply to being a faceless professional… The intellectual is an individual endowed with a faculty for representing, embodying, articulating a message, a view, an attitude, philosophy or opinion to, as well as for, a public. And this role has an edge to it, and cannot be played without a sense of being someone whose place it is publicly to raise embarrassing questions, to confront orthodoxy and dogma (rather than to produce them), to be someone who cannot easily be co-opted by governments or corporations, and whose raison d’etre is to represent all those people and issues that are routinely forgotten or swept under the rug. The intellectual does so on the basis of universal principles: that all human beings are entitled to expect decent standards of behavior concerning freedom and justice from worldly powers or nations, and that deliberate or inadvertent violation of these standards need to be testified and fought against courageously.”

በሪትዝ ሐሳብ የሚስማሙት አለን ላይትማን የአደባባይ ምሁራንን በሦስት ይከፍሏቸዋል። ለላይትማን የአደባባይ ምሁር ማለት፣

“Such a person is often a trained in a particular discipline, such as linguistics, biology, history, economics, literary criticism, and who is on the faculty of a college or university. When such a person decides to write and speak to a larger audience than their professional colleagues, he or she becomes a “public intellectual.””

ደረጃ አንድ፡ በዚህ ደረጃ የሚመደቡት ምሁራን የሚጽፉትም ሆነ የሚናገሩት ስለራሳቸው ጠባብ የጥናት ዘርፍ ብቻ ነው። ይህም ለሕዝቡ ፋይዳ ያላቸውን ጉዳዮች በጥልቀት በማብራራት በኩል በጣም ጠቃሚ ነው። ሰዎቹ የጥናት ክልላቸውን ድንበር በምንም መልኩ ተሻግረው አይገኙም።

ደረጃ ሁለት፡ ወደዚህ ደረጃ የተሸጋገሩ ምሁራን ከራሳቸው ጠባብ የጥናት ዘርፍ ተነስተው ጉዳዩ ያለውን ማኅበረሰባዊ፣ ባህላዊ እና ፖለቲካዊ ፋይዳ አስመልክተው ይጽፋሉ፣ ይናገራሉ።

ደረጃ ሦስት፡ በዚህ ደረጃ የሚደርሱ ምሁራን እንደ ምልክት መቆጠር ይጀምራሉ። ከጥናት ዘርፋቸው የሰፋና የበለጠ ትልቅ ሐሳብን የሚወክሉ ግዙፍ ስብእና ይላበሳሉ። ስለዚህም ከጥናት ዘርፋቸው ውጭ ባሉ ነገር ግን የላቀ ዋጋ ባላቸው ማኅበረሰባዊ፣ ፖለቲካዊ ወዘተ ጉዳዮች ላይ እንዲናገሩ እና እንዲጽፉ ይጋበዛሉ። የሚሰጡዋቸው ሐሳቦችም የምር ይወሰዳሉ። ጸሐፊው አንስታይን በፖለቲካ፣ በትምህርት፣ በፍልስፍናና በመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ሳይቀር አስተያየቱን ይጠየቅ እንደነበር በምሳሌነት ያነሳሉ።

ይህ የምሁራን “ድንበር ዘለል” የአደባባይ ተሳትፎ ትንተና በሌላ ሊተካም ሆነ ሊሻሻል የሚችል ነው። ቁም ነገሩ ግን አይለወጥም፤ ምሁራን በማኅበረሳቸው ውስጥ የሚኖራቸው ሚና የተለያየ ደረጃ ያለው መሆኑ። እርግጥ አንድ የተማረ ሰው ከምንም ተነስቶ ወደ መጨረሻው ደረጃ ለመድረስ የሚያስችለው ውጫዊ ሁኔታ ከጊዜ ጊዜ፣ ከቦታ ቦታ ይለያያል። ይሁንና እጅግ ወሳኙ ግብአት የግለሰቦቹ ውስጣዊና ግላዊ እምነት፣ ፍላጎት እና ግብ ነው። ቀድሞውኑ የምሁራኑ መገለጫ ነባራዊውን/ያለውን እያጸደቁና እያደነደኑ መኖር ሳይሆን ለሰው ልጅ የተሻለ ሕይወት ለማምጣት ያለውን መለወጥ/መረበሽ ነውና ውጫዊ ሁኔታው ከጅምሩ አጋዣቸው እንዲሆን አይጠበቅም። ይህም ሸክሙን ከውጭ ወደ ውስጥ ይመልሰዋል።

የእኛ የሕዝባዊ ምሁራን እነማን ናቸው? በእኔ ዕድሜ (የላይትማንን ደረጃ ልጠቀምና) ወደ ሦስተኛው ደረጃ መድረስ ችለው የነበሩ የአደባባይ ምሁር ፕሮፌሰር መስፍን ብቻ ናቸው። አሁን ደግሞ ጊዜው አጭር ቢሆንም ዶክተር ዳኛቸው አሰፋ ናቸው። የፕሮፌሰር መስፍን ወደ ፓርቲ ፖለቲካ መግባት (በተለይም የቅርብ ጊዜው የውዝግብ ድራማ) የሚያስነሳው ጥያቄ ቢኖርም ሰውየው ከአደባባይ ምሁርነታቸው የወረዱ አይመስለኝም። ምናልባትም አጋጣሚው የአደባባይ ምሁራንን በፓርቲ ፖለቲካ የሚኖራቸውን ተሳትፎ እንድንቃኝ የሚጠይቅ ነው። ነጻነት ባለበት የምእራቡ ዓለም ያሉና የአደባባይ ምሁር (public intellectual) መባል የሚገባቸው ጸሐፊዎች፣ ተናጋሪዎችም አሉ፣ ቁጥራቸው የእድሉን ያህል አይደለም እንጂ።

ሪትዝን የመሰሉ ጸሐፊዎች የአደባባይ ምሁርነትን ያለውን/ገዢውን አመለካከትና አሰራር በመቃወም ጭምር መለካት እንዳለበት ያምናሉ። ይህም ተቃውሞው ርእዮተ ዓለማዊ፣ የፖሊሲ፣ የአፈጻጸም (አንዱን ወይም ሌላውን) ገጽታ እንደሚኖረው ግልጽ ነው። ይህ ማለት ግን የግድ የተቃዋሚ ፓርቲ ደጋፊነትን የሚጠይቅ ተደርጎ መወሰድ አይችልም፤ በመሠረቱ የገዢው ቡድን/አመለካከት ደጋፊ ሆኖም ለውጥን ማቀንቀን ይቻላል። የዚያኑ ያህልም ገዢውን ፓርቲ መቃወም ምሁራዊ አስተዋጽኦን/ደረጃን የሚቀንስ አለዚያም የተቃዋሚ ፓርቲ ታማኝ ደጋፊ ብቻ አድርጎ የሚያስቆጥር ሊሆን አይችልም።

እያወቁ እንዳላወቁ፣ እያዩ እንዳላዩ፣ እየሰሙ እነዳልሰሙ ሆኖ፣ በለሆሳስ ማንጎራጎር፤ በራስ ዝምታ ውስጥ መቀበር የዘመኑ ፈሊጥ ሆኗል። ይህም ቢሆን ከባድ የመሰላቸው ደግሞ “አንድ ቀንን” እየጠበቁ ንጉሡ መስማት የሚፈልጉትን እየዘፈኑ ቢያንስ ምትሐታዊ ውጫዊ ሰላም ለመፍጠር ይሞክራሉ። የቀሩት ደግሞ በንጉሡ ዙፋን ዙሪያ ተሰብስበው በየቋንቋቸው፣ በየሞያቸው “ሺህ ዓመት ንገሥ” ይላሉ፤ የሺህ ዓመቱ መንግሥት ስለፈጠራት/ስለሚፈጥራት ምድራዊ ገነት ምሁራዊ ቡራኬ ይሰጣሉ፤ “ከዚህ በላይ ምን ትፈልጋላችሁ?” ሲሉ ምሁራዊ ተሳልቆ ያሰማሉ።

ለዚህ ጽሑፍ አስተያየት በመስጠት የመጀመሪያ ይሁኑ!

Leave a Reply

You must be to post a comment.

በምግብ እጥረት ለተጠቁ ወገኖች 20 ሚሊዮን ዶላር ርዳታ ተጠየቀ

-በሴፍቲኔት ፕሮግራም ምግብ ለሥራ የታቀፉ ዜጎች ቁጥር በሦስት መቶ ሺህ ጨምሯል

-ለምግብ እጥረት የተጋለጡ ዜጎችቹ ቁጥር ተአማኒነት የጎደለው ነው ተብሏል

This post is available in: ኸንግሊስህ

(ሙሉ ገ)

በምግብ እጥረት ለተጎዱ ዜጎች ከምግብ እርዳታ ውጪ 20 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር የእርዳታ ድጋፍ ያስፈልገኛል ሲል የግብርና ሚንስቴር ለለጋሽ አገሮች እና ለእርዳታ ድርጅቶች አስታወቀ።

ህዳር 15 ቀን 2003 ዓ.ም በቀድሞው አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኤጀንሲ መሰብሰቢያ አዳራሽ ከቀኑ በ10፡00 ሰዓት ላይ ለለጋሽ አገሮችና ለጋዜጠኞች በተሰጠው መግለጫ ላይ የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ምትኩ ካሳ የተረጂው ቁጥር ወደ ሁለት ሚሊዮን ሦስት መቶ ሺ ወርዷል ብለዋል፡፡  የአማራ እና ሌሎች ክልሎች ሪፖርትና ዳታ በወቅቱ ባለመድረሱ ይቅርታ የጠየቁት ሚንስትር ዴኤታ አቶ ምትኩ ካሳ ከሁለት ሚሊዮን ሦስት መቶ ሺህ ከተገመቱት ተረጂዎች ውስጥ፣ 29.2 በመቶ ከሶማሌ ክልል፣ 29 ከመቶው ከትግራይ ክልል እና 26.3 በመቶ ከኦሮሚያ ክልል መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በ2002/03 ዓ.ም ምርት ዘመን በነበረው የተሻለና ለግብርና ሥራ እንቅስቃሴ አመቺ ሆኖ የተገኘ የበልግና የመኸር ዝናብን ተከትሎ በእርዳታ ፈላጊ አካባቢዎች ያለው የምግብ ዋስትና ሁኔታ በመጠኑ የተሻሻለ ቢሆንም፣ ገና የአማራና ሌሎች ክልሎች ዳታ በአግባቡ ባልተሰበሰበበት ሁኔታ በአገሪቱ የዕለት የምግብ እርዳታ ፈላጊ ቁጥር ቀንሶ ወደ 2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሕዝብ ዝቅ ብሏል ተብሎ በመንግሥት የተሰጠው የችኮላ ድምዳሜ ትልቅ ግነት እንዳለበት ይሰማኛል በማለት አዲስ ነገር ያነጋገራቸው የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የዜና ምንጭ ገልጸውልናል፡፡

እኝሁ በግብርና ሚኒስቴር በቅድሚያ ማስጠንቀቂያ ምላሽ ዳይሬክቶሬት ውስጥ የሚሠሩ የዜና ምንጫችን እንደነገሩን በተያዘው የፈረንጆች ዓመት በኢትዮጵያ በሴፍቲኔት ፕሮግራም ምግብ ለሥራ የታቀፉ ዜጎች ቁጥር በሦስት መቶ ሺህ መጨመሩን ገልጸውልናል፡፡

እንደ ዜና ምንጮቻችን ገለጻ “ በምግብ ለሥራ ፕሮግራም”  የታቀፉ የገጠር ነዋሪዎች ከ7 ነጥብ 5 ወደ 7 ነጥብ 8 ሚሊዮን ያሻቀበው ከዚህ በፊት በሴፍቲኔት ምግብ ለሥራ ፕሮግራም ታቅፈው የማያውቁ በአፋር እና በሶማሌ ክልሎች ያሉ ወረዳዎች በምግብ እጥረት በመጠቃታቸው ነው፡፡   በርካታ ሕዝብ በየዓመቱ ተጨማሪ የአስቸኳይ ጊዜ የዕለት የምግብ እርዳታ አቅርቦት ድጋፍ የሚፈልግ ነው ያሉን የዜና ምንጫችን፣ በተያዘው የፈረንጆች ዓመት (2010 እ.ኤ.አ) በተደረገ የዳሰሳ ጥናት 5 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን የዕለት እርዳታ ድጋፍ አቅርቦት የሚሹ ኾነው የተገኙ ናቸው ብለውናል፡፡

በኢትዮጵያ በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች በተለያዩ ጊዜያት የዜጎችን ሕይወት የሚቀጥፍ ሲሆን፣ ከ1986 ዓ.ም ጀምሮ ብሔራዊ የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት ፖሊሲ ሥራ ላይ ቢውልም ለውጥ ማምጣት ባለመቻሉ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ በግብርና ሚኒስቴር ሥር ተጠቃሎ ሥራውን እንዲያከናውን ተደርጓል፡፡

No Responses to “በምግብ እጥረት ለተጠቁ ወገኖች 20 ሚሊዮን ዶላር ርዳታ ተጠየቀ”

  1. WEHA BEWKTUT EMOCHEEEE…..

  2. This news is intended to give the impression to the readers that the rhetoric of economic development is ridiculous.
    Just out of curiosity, has anyone ever seen any positive news about Ethiopia on ANO?

  3. man neber kahun behuala etiban yemibal neger anteyikim yalew_….tiyake milikit ….

Leave a Reply

You must be to post a comment.

በዲላ ዩኒቨርስቲ በተቀሰቀሰ ሁከት ተማሪዎች ተጎዱ

ከትላንት ጠዋት ጀምሮ “መጀመሪያ ልጅቷ ትፈለግ! አትኩሮት ታግኝ!” በሚል ትምህርት ያለመማር እና ምግብ ያለመመገብ አድማ የመቱት ተማሪዎች ሁከት ፈጥረው መስታዎቶችን በመሰባበር የመማር- ማስተማር ሂደቱን በማስተጓጎል፣ በምሳ ሰዓት ላይ ምግብ ለመመገብ ካፌ ከገቡ ተማሪዎች ጋራ በተፈጠረ ግርግር ቁጥራቸው በውል ባልታወቀ ተማሪዎች ላይ የመፈንከት አደጋ ደርሶባቸዋል። በመስታዎት የመቆረጥ እና በግርግሩ እና በተቃውሞው በተነሳው ሁከት የመረጋገጥ አደጋ ደርሶባቸው ወደ ሆስፒታል የተወሰዱ ተማሪዎች እንደነበሩም አንድ የተማሪ ካውንስል የአመራር አባል ለሪፖርተራችን አስረድቷል።

This post is available in: ኸንግሊስህ

(ሙሉ ገ.)

ብዙነሽ ብርሃኑ የተባለች የሦስተኛ ዓመት የታሪክ ዲፓርትመንት ተማሪ በዋናው ዩኒቨርስቲ ግቢ ውስጥ አድራ ወደ አዲሱ ሰመራ ካምፓስ ከ15 እስከ 20 ደቂቃ የሚያስጉዘውን መንገድ ቅዳሜ ህዳር 4 ቀን 2003 ዓ.ም ስታቋርጥ ዋለሜ በተባለው ወንዝ ውስጥ ሰጠመች። ይህንኑ የመስጠም አደጋ ተማሪዎች ለዩኒቨርስቲው አስተዳደር ሪፖርት ካደረጉ በኋላ ልጅቷን በሕይወት ለማትረፍም ኾነ አስከሬኗን ለማግኘት ፈጣን የኾነ ምላሽ ባለማግኘታቸው ምክንያት ባነሱት የተቃውሞ ድምፅ  በዩኒቨርሲቲው ውስጥ ሁከቱ እንደተቀሰቀሰ አንድ የዩኒቨርሲቲው መምህር ለአዲስ ነገር ሪፖርተር በስልክ አስረድተዋል።

ትላንት ሕዳር 8 ቀን 2003 ዓ.ም ረፋድ ላይ በዲላ ዩኒቨርስቲ ውስጥ በተፈጠረው በዚሁ የተማሪዎች ሁከት ምክንያት የተፈነከቱ ተማሪዎችም ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል። ከዚህም በተጨማሪ በሁከቱ የዩኒቨርሲቲው መስኮቶች እና በሮች ተሰባብረዋል፤  የመመገቢያ ቁሳቁሶች ወድመዋል፤ በአካባቢው ፌዴራል ፖሊስ ጣልቃ በመግባት ግቢውን ተቆጣጥሯል።

እንደ መምህሩ ገለጻ ለተማሪዎቹ ቁጣ መቀስቀስ ምክንያት የኾነውን የተማሪ ብዙነሽን አስከሬን ለማግኘት እና ለማውጣት ዲላ ዩኒቨርስቲ የአካባቢውን ዋናተኞች እየተጠቀመ ቢኾንም ዋናተኞቹ ወንዙ የአምልኮ ሥርዐት የሚካሄድበት እና በየዓመቱም የሰው ግብር የሚበላ ነው በማለት ወደ መሀል እና ወደ ታች ዘልቀው ለመግባት ድፍረት በማጣታቸው ሳይሳካ እንደቀረ  ጨምረው ገልጸዋል።

ከትላንት ጠዋት ጀምሮ “መጀመሪያ ልጅቷ ትፈለግ! አትኩሮት ታግኝ!” በሚል ትምህርት ያለመማር እና ምግብ ያለመመገብ አድማ የመቱት ተማሪዎች ሁከት ፈጥረው መስታዎቶችን በመሰባበር የመማር- ማስተማር ሂደቱን በማስተጓጎል፣ በምሳ ሰዓት ላይ ምግብ ለመመገብ ካፌ ከገቡ ተማሪዎች ጋራ በተፈጠረ ግርግር ቁጥራቸው በውል ባልታወቀ ተማሪዎች ላይ የመፈንከት አደጋ ደርሶባቸዋል። በመስታዎት የመቆረጥ እና በግርግሩ እና በተቃውሞው በተነሳው ሁከት የመረጋገጥ አደጋ ደርሶባቸው ወደ ሆስፒታል የተወሰዱ ተማሪዎች እንደነበሩም አንድ የተማሪ ካውንስል የአመራር አባል ለሪፖርተራችን አስረድቷል።

ትላንት ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ በርካታ የመንግሥት የደኅንነት እና የመረጃ ሠራተኞች እንዲሁም የድንጋይ መከላከያ ሙሉ ትጥቅ ያደረጉ የፌዴራል ፖሊስ አባላት ዋናውን ግቢ ከተቆጣጠሩ በኋላ ለሁለት ተከፍለው የነበሩት ተማሪዎች አንድ ላይ በመኾን ተቃዉሟቸውን ሲገልጹ ነበር። ፌዴራል ፖሊስ ተቃውሟቸውን ሲገልጹ የነበሩትን ተማሪዎች ቀስ በቀስ ከግቢው እንዲወጡ በማድረግ ከግቢው ውጭ እንዲቀመጡ አድርጓቸዋል።

ማምሻውን ይህን ዜና እስከምናጠናክርበት ጊዜ ድረስ ተማሪዎች በዩኒቨርስቲው ካፌ መመገባቸውን አቁመው በጩኸት አና በመዝሙር ቁጣቸውን እየገለጹ ሲኾን ፌዴራል ፖሊስም ከግቢው ውስጥ በተጠንቀቅ እየጠበቀ ነው። የሦስተኛ ዓመት የታሪክ ተማሪ የነበረችው ብዙነሽ ብርሃኑ ቤተሰቦቿ በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ክፍለ አገር እንደሚገኙም ለማወቅ ተችሏል።

2 Responses to “በዲላ ዩኒቨርስቲ በተቀሰቀሰ ሁከት ተማሪዎች ተጎዱ”

  1. WEHA BEWKTUT EMOCHEEEE…..

  2. This news is intended to give the impression to the readers that the rhetoric of economic development is ridiculous.
    Just out of curiosity, has anyone ever seen any positive news about Ethiopia on ANO?

  3. man neber kahun behuala etiban yemibal neger anteyikim yalew_….tiyake milikit ….

Leave a Reply

You must be to post a comment.

[አንድ ለቅዳሜ] የፖለቲካ ተሐድሶን ፍለጋ

ጥያቄውን በአቋራጭ ለመመለስ ቀላሉ መፍትሔ “አንድ ብቸኛ የተሐድሶ አነሳሽ ሊኖር አይችልም” ብሎ ውይይቱን በአጭሩ መቅጨት ነው። አለዚያም ፖለቲካችን ዞሮ ዞሮ የአፍሪካ ፖለቲካ ስለሆነ አለዚያም “ያልተጠበቀ ነገር” ወይም “ተአምር” ሊፈጠር እንደሚችል በማመን መልሱን ለጊዜ መተው አማራጭ መልስ ይመስል ይሆናል። ሁለቱም የአጭር መልስ አማራጮች ፖለቲካችን የገባበትን ድቅድቅ ከማሳየታቸውም ባለፈ ቀላል መከራከሪያዎች ተደርገው የሚታዩ አይደሉም። እነዚህን ለጊዜው ትተን ግን አሁን በማኅበረሰባችን ውስጥ ካሉ ኀይሎች/ክፍሎች መካከል ቀጣዩን የፖለቲካ ተሐድሶ በመቀስቀስ የትኛው ምን አይነት አቅም እና ዕድል እንዳለው መገምሙ ጠቃሚ ይሆናል።

1. አገር ውስጥ የሚገኙ ተቃዋሚዎች?
2. የተማረው ኀይል (ተማሪዎችን ጨምሮ)
3. የተደራጁ አካላት (ሲቪል ማኅበራት፣ የሞያ ማኅበራት ወዘተ)?
4. በሥልጣን ላይ በሚገኘው ቡድን ውስጥ የሚገኙ/የሚፈጠሩ ንዑስ ቡድኖች?
5. የታጠቁ ተቃዋሚ ኀይሎች
6. በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን (ዳያስፖራ)
7. ክፍለ አህጉራዊ ሁኔታዎች
8. የውጭ ተጽእኖ (በተለይ የምዕራቡ ዓለም እና ቻይና)
9. ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች

(እዚህ ያልተቀሰ ቢኖር እየጨመርን እንደምንቀጥል ታሳቢ በማድረግ) ከእነዚህ መካከል ቀጣዩን የፖለቲካ ተሐድሶ በማስጀመርና በመምራት በተናጠልም ሆነ በጋራ ወሳኝ ድርሻ የሚኖራቸውን ሦስት አካሎች በቅደም ተከተል ምረጡ ብንባል መልሳችን ምን ይሆናል?

This post is available in: ኸንግሊስህ

የኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሽግግር በብዙ መልኩ ከማይላወስበት ቅርቃር ውስጥ ገብቷል። መሠረታዊ ፖለቲካዊ ተሐድሶ (Political Reform) እንደሚያመጣ ተስፋ የተጣለበት ኢሕአዴግ በቀዳሚዎቹ ዓመታት ያደረጋቸውን ለውጦች ሳይቀር መልሶ እያጠፋ በኋላ ማርሽ መጓዝን መርጧል። በአጠቃላይ ሲታይም ኢትዮጵያ አዲስ የፖለቲካ ተሐድሶ እንደሚያስፈልጋት ግልጽ ነው። አሁን ለመወያየት ጭምር ቀላል ሆኖ የማይታየው “ቀጣዩ የፖለቲካ ተሐድሶ በወሳኝነት የሚመጣው ከየት እና እንዴት ነው?” የሚለው ጥያቄ ነው።

ጥያቄውን በአቋራጭ ለመመለስ ቀላሉ መፍትሔ “አንድ ብቸኛ የተሐድሶ አነሳሽ ሊኖር አይችልም” ብሎ ውይይቱን በአጭሩ መቅጨት ነው። አለዚያም ፖለቲካችን ዞሮ ዞሮ የአፍሪካ ፖለቲካ ስለሆነ አለዚያም “ያልተጠበቀ ነገር” ወይም “ተአምር” ሊፈጠር እንደሚችል በማመን መልሱን ለጊዜ መተው አማራጭ መልስ ይመስል ይሆናል። ሁለቱም የአጭር መልስ አማራጮች ፖለቲካችን የገባበትን ድቅድቅ ከማሳየታቸውም ባለፈ ቀላል መከራከሪያዎች ተደርገው የሚታዩ አይደሉም። እነዚህን ለጊዜው ትተን ግን አሁን በማኅበረሰባችን ውስጥ ካሉ ኀይሎች/ክፍሎች መካከል ቀጣዩን የፖለቲካ ተሐድሶ በመቀስቀስ የትኛው ምን አይነት አቅም እና ዕድል እንዳለው መገምሙ ጠቃሚ ይሆናል።

1. አገር ውስጥ የሚገኙ ተቃዋሚዎች?

2. የተማረው ኀይል (ተማሪዎችን ጨምሮ)

3. የተደራጁ አካላት (ሲቪል ማኅበራት፣ የሞያ ማኅበራት ወዘተ)?

4. በሥልጣን ላይ በሚገኘው ቡድን ውስጥ የሚገኙ/የሚፈጠሩ ንዑስ ቡድኖች?

5. የታጠቁ ተቃዋሚ ኀይሎች

6. በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን (ዳያስፖራ)

7. ክፍለ አህጉራዊ ሁኔታዎች

8. የውጭ ተጽእኖ (በተለይ የምዕራቡ ዓለም እና ቻይና)

9. ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች

(እዚህ ያልተቀሰ ቢኖር እየጨመርን እንደምንቀጥል ታሳቢ በማድረግ) ቀጣዩን የፖለቲካ ተሐድሶ በማስጀመርና በመምራት በተናጠልም ሆነ በጋራ ወሳኝ ድርሻ የሚኖራቸውን ሦስት አካሎች በቅደም ተከተል ምረጡ ብንባል መልሳችን ምን ይሆናል?

***************

[በነገራችን ላይ]

የብዙ ሰዎች አትኩሮት የአውሮፓ ኅብረት የምርጫ ታዛቢ ልኡክ ባወጣው የመጨረሻ ሪፖርት ላይ እንደሰነበት ግልጽ ነው። አንባቢዎቻችን ይህ አትኩሮት የሸፈነው ሌላ ምርጫ ነክ ዜና እንዳያመልጣቸው ማስታወስ አግባብ መሰለኝ። የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ “ድኅረ ምርጫ የዳሰሳ ጥናት” እያደረገ መሆኑን አስታውቋል። ጥናት መደረጉ መልካም ሐሳብ ነበር። የጥናቱን ውጤት ከወዲሁም መገመት ስለሚቻል ብዙ የሚያነጋግር አይደለም። ቁም ነገሩ ወዲህ ነው።

የዳሰሳ ጥናቱ “በሁሉም የክልል መስተዳድሮችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች በሚገኙ በ77 የዞን መስተዳድሮች ለናሙና በተመረጡ 154 የምርጫ ክልሎች ይካሄዳል፡፡ በተመሳሳይም በተመረጡ 916 የምርጫ ጣቢያዎች ከእያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ 15 መራጮች ናሙና ተወስዶ በጠቅላላው ከ13 ሺህ መራጮች በላይ በጥናቱ ይካተታሉ፡፡…ለጥናቱ መረጃ የመሰብሰብ ሥራ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅና ይህንን ሥራ የሚያከናውኑ ቡድኖች በሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ካለፈው ጥቅምት 29 ቀን 2003 ጀምሮ ተሰማርተል፡፡”

13 ሺህ ሰዎች በመላ አገሪቱ የሚጠየቁበት ጥናት በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል። ኢትዮጵያ እንዴት አይነት ለጥናት የተመቸች አገር ብትሆን ነው 13 ሺህ ሰዎችን ለጥናት ግብአት ለማነጋገር አንድ ወር ብቻ የሚበቃው? የጥናት አቅማችን በየዓመቱ ስንት እያደገ ይሆን? የምስራች ነው።

ለዚህ ጽሑፍ አስተያየት በመስጠት የመጀመሪያ ይሁኑ!

Leave a Reply

You must be to post a comment.

ተማሪዎቹ በረሀብ የተጠቁበት ረጲ ትምህርት ቤት መንግሥት እርዳታ አላረገልኝም አለ

This post is available in: ኸንግሊስህ(ሙሉ ገ) በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍል ከተማ የሚገኘው ረጲ የመጀመርሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት በረኀብ ለተጠቁት ተማሪዎቹ ርዳታ በማድረግ ላይ የሚገኙት መምህራን እና በጎ አድራጊ ግለሰቦች እንጂ መንግሥት እና መያዶች አይደሉም ሲል ለአዲስ ነገር ገለጸ። በረኀቡ ጥቃት የደረሰባቸውን ሕጻናት በሚመግበው ማዕከል ውስጥ የሚሠሩ አንድ አስተባባሪ ለአዲስ ነገር እንደገለጹት ተማሪዎቹን ቋሚ [...]

This post is available in: ኸንግሊስህ

(ሙሉ ገ)

በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍል ከተማ የሚገኘው ረጲ የመጀመርሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት በረኀብ ለተጠቁት ተማሪዎቹ ርዳታ በማድረግ ላይ የሚገኙት መምህራን እና በጎ አድራጊ ግለሰቦች እንጂ መንግሥት እና መያዶች አይደሉም ሲል ለአዲስ ነገር ገለጸ።

በረኀቡ ጥቃት የደረሰባቸውን ሕጻናት በሚመግበው ማዕከል ውስጥ የሚሠሩ አንድ አስተባባሪ ለአዲስ ነገር እንደገለጹት ተማሪዎቹን ቋሚ እና ወጥ በኾነ መንገድ በመመገብ ከችግሩ ለማውጣት የሚያስችል ኹኔታ ባለመኖሩ ለጊዜው ረኀቡ ለጸናባቸው 261 ሕጻናት ብቻ ቁርስ እና ምሳ እየመገቡ በማስተማር ላይ ናቸው።

በረኀብ እየተዳከሙ እና እየተዝለፈለፉ ትምህርታቸውን መከታታል ያሉትን ተማሪዎች ከሁለት ሳምንት በፊት የአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቭዥን ለዕይታ ካበቃው በኋላ የክፍለ ከተማው ሥራ አስኪያጅም ኾነ የከተማዋ ከንቲባ እስከ አሁን ድረስ አልጎበኟቸውም፤ ልጆቹ ላሉበት ችግር መፍትሄ ለማምጣት ከመንግሥት ምንም ዐይነት ምላሽ አላገኘንም ብለው የሚናገሩት እኚሁ መምህር ከአንዳንድ መንግሥታዊ ካልኾኑ ድርጅቶች ግን ተስፋ ሰጭ የኾነ ምልክት ማየታቸውን ገልጸዋል።

አንዳንዶቹ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ለአጭር ጊዜ የሚኾን መፍትሄ እንደሚያፈላልጉ ቃል የገቡ ሲኾን ሌሎቹ ደግሞ ዘላቂ የኾነ መፍትሄ ለማምጣት የሕጻናቱን ትክክለኛ ቁጥር እና የቤተሰባቸውን የኋላ ታሪክ የማዕከሉ ኀላፊዎች እንዲያዘጋጁላቸው እንደጠየቋቸውም አስረድተዋቸዋል።

ይህ በተማሪዎቹ ላይ መተደጋጋሚ ይታይ የነበረ ችግር የአዲስ አበባ መስተዳድር ቴሌቭዥን እስኪያሰራጨው ድረስ የትምህርት ቤቱን መምህራን እና አስተዳደር ለረዥም ጊዜ ሲያስጨንቅ የኖረ እንደ ነበር የሚያስረዱት መምህሩ አሁን የመጡት ግለሰቦች በእያንዳንዳቸው 4ኪሎ መኮረኒ፣ 10 ኪሎ ሩዝ እና ዳቦዎችን እንዲሁም የተለያዩ ዐይነት ምግቦችን በማምጣት እና በማብሰል ለመመገብ እየሞከሩ እንደኾኑም አስረድተዋል።

እስከ ሕዳር 2 ቀን 2003 ባሉት ቀናት ከ 4ሺሕ እስከ 15 ሺሕ ብር ድረስ ግለሰቦች ያዋጡ ሲኾን በአጠቃላይ 20 ሺሕ ብር ለማግኘት እንደተቻለም ታውቋል። በትምህርት ቤቱ ውስጥ ለዚሁ ረኀብ የተጋለጡት ልጆች ዕድሜያቸው ከ 7 ዓመት እስከ 16 ዓመት  ያሉትን እንደኾነም መምህራኑ ለአዲስ ነገር አስረድተዋል።

በአጠቃላይ ሲታይ የአብዛኞቹ ተማሪዎች ቤተሰቦች የቀን ሠራተኞች፣ የወር ገቢያቸው ለምግብ እንኳ መሸፈን የማይችል (እጅግ አነስተኛ) የኾነ፣ ጡረተኞች፣ አቅመ ደካሞች እና ቤተሰቦቻቸውን በኤችአይቪ ምክንያት በሞት የተነጠቁ ሲኾኑ “የተራበው የቤተሰብ ወኪል” ናቸውም ሲሉ ተናግረዋል።

ይህ በተማሮዎች ላይ የታየው በረኀብ የመዝለፍለፍ አደጋ በድንገት የመጣ ሳይኾን ከዛሬ አራት ዓመት ጀምሮ ምልክቱ ይታይ እንደነበር የገለጹት የትምህርት ቤቱ ሠራተኛ በ2002 ዓ.ም አንድ የርዳታ ክበብ በማቋቋም ተማሪዎቹን ለማገዝ ባደረገው እንቅስቃሴ ከአንድ የግል ትምህርት ቤት በተገኘ የ14 ሺሕ አምስት መቶ ብር ርዳታ ድጋፉን ቢቀጥልም በዘንድሮው የትምህርት ዘመን የሚራቡት ሕጻናት ቁጥር እስከ 500 በመድረሱ የመማር ማስተማር ሂደቱን እንዲስተጓጎል እና ከቁጥጥር ውጭ እንዲወጣ እንዳደረገው ይገልጻሉ።

ከ1999 ዓ.ም ጀምሮ መታየት የጀመረው ይኸው የመራብ ችግር በዚያ ሰዓት በ31 ተማሪዎች ላይ በተደጋጋሚ ክፍል ውስጥ የመተኛት፣ የመዳከም እና የመዝለፍለፍ ምልክት ያሳይ ነበር። ይህን ችግር ለመቅረፍ መምህራኑ የመጀመርያ ርምጃ አድርገው የወሰዱት በየግላቸው የቻሉትን ያህል ተማሪ ለመመገብ መሞከር እንደነበር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ለዚህ ጽሑፍ አስተያየት በመስጠት የመጀመሪያ ይሁኑ!

Leave a Reply

You must be to post a comment.

በ“አምቼዎች” ዓለም ውስጥ፡ ፖለቲካ ፣ ማንነት እና ስደት

(ልዩ ጥንቅር)
አምቼነት ከኤርትራ ጋራ ብቻ አይቆራኝም። ከኢትዮጵያ በተለይም ከአዲስ አበባ ጋራ ባለው ጥልቅ ትሥሥርም ይገለጻል። አሥመራ ላይ “አምቼዎች” በነገረ ሥራቸው ተለይተው ይታወቃሉ። “ብዙ ኤርትራውያን አማርኛ ቋንቋን የሚናገረው አማራ ብቻ ይመስላቸው ነበር። ከ1990 ዓ.ም በኋላ ብዛት ያላቸው አምቼዎች ከኢትዮጵያ ተባርረው አሥመራን አጥለቀለቋት” ይላል ቢኒያም። ከዚያ በኋላ አምቼዎችን አሥመራ ውስጥ ለመለየት ቀላል ነበር። አማርኛ የሚናገሩ፣ በአረማመዳቸው፣ በአለባበሳቸው፣ በአንጻራዊ መልኩ በተላበሱት ግላዊ ነጻነት ይታወቃሉ። የአማርኛ ሙዚቃ በአሥመራ እንግዳ በኾነ መልኩ በስፋት የሚያዳምጡትም አምቼዎች ነበሩ።

addis ababa

This post is available in: ኸንግሊስህ

የማኅደረ ጊላይ የለጋነት ዕድሜ እንዲሁ እንደ ዐይን ጥቅሻ እያለፈ ነው። ወደ ኋላ ተመልሶ ሲያስብ ደስ የሚል ነገር ትዝ አይለውም።ሕይወት ልክ ከማለዳ ጣፋጭ እንቅልፍ እንደሚያባንኑት አስፈሪ የልጅነት የተረት ጭራቆች የተሞላች ትመስለዋለች::  ተረት የሚመስሉ ታሪኮችን እየኖረ፣ እየሰማ እና እየታዘበ እዚህ ደርሷል። መባረር፣ ስደት፣ ሞት… እና በትዝታ መዋትት በሕይወቱ ውስጥ እስካሁንም ይገለባበጣሉ።

የናይሮቢ እምብርት

ሰሞኑን ከናይሮቢ 500 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የካኩማ ስደተኞች ካምፕ ወደ ኬኒያ መናገሻ ከተማ ብቅ ብሏል። ለእርሱ ጉዞ አዲስ አይደለም፤ ስንቱን ተጉዟል። ገና የዐሥራዎቹን አጋማሽ በቅጡ ሳይደፍን ከተወለደባት እና አፈር ፈጭቶ ካደገባት አዲስ አበባ እስከ አሥመራ ያለውን 1176 ኪሎ ሜትር አይረሴ ጉዞ አድርጓል። ጉዞው ግን እንደዚህኛው በፍቃዱ የተደረገ አልነበረም። ያልተጠበቀ እና በስሜት ምስቅልቅል የተሞላ ነበር።  ደም አፋሳሹ እና ትርጉም የለሹ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲነሳ ከኢትዮጵያ ተባርሮ አሥመራ ገባ።  ከአባቱ ጋር።

ትውልደ “ኤርትራዊ” በመኾናቸው ምክንያት የመባረር ዕጣ እንደገጠማቸው የስሚ ስሚ ቢሰማም ለጋ ዕድሜው ከአባቱ ጋራ የተባረረበትን ምክንያት በቅጡ እንዳይረዳው አድርጎት ነበር። “እኔ በወቅቱ እንኳን በሩቅ የማውቃትን ኤርትራን ቀርቶ ተወልጄ ያደግኩባት ኢትዮጵያዊ ዜግነት ምን እንደሚመስል የማሰላስልበት ብስለት ላይ አልደረስኩም። ከትልቁ የዜግነት ጉዳይ ይልቅ የሠፈር ልጅነት ለእኔ ትርጉም ነበረው” ሲል ወደ ኋላ ተመልሶ ያስታውሳል። “‘የጨርቆስ ልጅ’ መባል ያኮራ ነበር” ይላል ማኅደረ የልጅነት ጣፋጭ ጊዜውን ያሳለፈበትን ሰፈር እያሰበ። “የጨርቆስ ልጅነቴን የምገልጸውን ያህል እንኳ ዜግነት የሚባለው ነገር ሳይገባኝ ነው አሻግረው “አባ ሻውል”(አስመራ ውስጥ የሚገኝ ሠፈር) የወረወሩኝ።”

ለማኅደረ የአዲስ አበባው ጨርቆስ እና የአሥመራው አባ ሻውል የሚመሳሰሉበት ነገር እንዳላቸው ታይቶታል። ሁለቱ ሰፈሮች ስማቸው ከድህነት ጋራ ተያይዞ ይጠራል። አባ ሻውል በምርጥ ፕላኗ በማትታማው አሥመራ ላይ ያለ ቢኾንም እንደ ጨርቆስ እና መሰል የአዲስ አበባ ሰፈሮች “የድኻ » የሚባል መንደር ነው።  ገዛ መንዳ ሐበሻ ከአባ ሻውል ጋራ የሚጠቀስ ሰፈር ነው-በአስመራ።  ልክ እንደ አዲስ አበባዎቹ የአራት ኪሎን አሮጌ ቄራ እና  የፒያሳው ሠራተኛ ሠፈር አይነት።

ማኅደረ አባ ሻውልን ለመልመድ አልተቸገረም። ድህነቱም፣ የ”አራዳ” ልጅነቱም ረድቶታል። ግን አንድ ነገር ሙሉ በሙሉ የአባ ሻውል ልጅ እንዳይኾን ልጓሙን ይይዝበታል። አዲሶቹ ጓደኞቹም እንደ አንዱ የሠፈራቸው ልጅ እንጂ የማንነታቸው አካል አድርገው ለመቁጠር አልፈቀዱም። “ለእነርሱ ኤርትራዊ አይደለሁም፤ ኢትዮጵያዊም አይደለሁም” ይላል። “ለእነርሱ ማኅደረ “አምቼ” ነው።  ብዙዎች የሚጠሩትም “አምቼው” እያሉ ነው።

“አምቼ”…? የምን አምቼ?

“ይኼን ስያሜ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት አባ ሻውል ላይ ነው” አለ ማኅደረ “ስለአምቼነቱ” የሰማበትን ቀን እያስታወሰ።“አንዱ ጓደኛዬ በጨዋታ ላይ እንዲህ አለኝ። “ኻብ ሠፈርካ ዕንታይ ከምዝብልካ ትፈልጥ ዶ?” (ምን እንደምታባል ታውቃለህ?) እኔ አዲስ መጤ ምን ሊሉኝ ይችላሉ በሚል ግርምት “አይፈልጥን” ብዬ መለሰኩለት። ያን ጊዜ “አምቼ” መኾኔን ነገረኝ።” የጓደኛውን ገለጻ ተከትሎ ማኅደረ ከሌሎች ኤርትራውያን “የተለየ ዜጋ” መኾኑ ይሰማው ጀመር። ማኅደረ አይወቀው እንጂ “አምቼ” የሚለው ስያሜ እርሱ አዲስ አበባ እያለ አገልግሎት ላይ ውሎ ነበር።

ቢኒያም ፍስሐ...

ጁባ የሚኖረው የ40 ዓመቱ ቢኒያም ፍስሐ ከኤርትራውያን ቤተሰቦቹ ጋራ የኖረው አዲስ አባባ 22 ማዞሪያ አካባቢ ነው። ቢኒያም “አምቼ” የሚለውን መጠሪያ በደርግ ጊዜ አዲስ አበባ እያለ መስማቱን ይናገራል። “ኢትዮጵያ ውስጥ ለተወለደ ኤርትራዊ የተሰጠ መጠሪያ ነበር። ቃሉ የሚገልጸው ኢትዮጵያ ውስጥ መገጣጠሙን ነው” ይላል። መጠሪያው በአንድ ወገን ኤርትራዊ ከኾኑ ወይም ከሁለት ኤርትራውያን ወላጆች ለተወለዱ ዜጎች የሚውል ነው። ስሙ የተወሰደው አዲስ አበባ ከሚገኘው እና በኢትዮጵያ መንግሥት እና በጣሊያኑ የመኪና አምራች ድርጅት ፊያት መካከል በተደረገው ስምምነት ከተቋቋመው “አምቼ”(AMCE) ኩባንያ ነው። የመኪናው አካላቶች ጣሊያን ተመርተው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚገጣጠሙ ሁሉ “አምቼዎች” ኢትዮጵያ ውስጥ “የተገጣጠሙ” የሚል ትርጓሜ ይሰጣል።

አምቼነት ከኤርትራ ጋራ ብቻ አይቆራኝም። ከኢትዮጵያ በተለይም ከአዲስ አበባ ጋራ ባለው ጥልቅ ትሥሥርም ይገለጻል። አሥመራ ላይ “አምቼዎች” በነገረ ሥራቸው ተለይተው ይታወቃሉ። “ብዙ ኤርትራውያን አማርኛ ቋንቋን የሚናገረው አማራ ብቻ ይመስላቸው ነበር። ከ1990 ዓ.ም በኋላ ብዛት ያላቸው አምቼዎች ከኢትዮጵያ ተባርረው አሥመራን አጥለቀለቋት” ይላል ቢኒያም። ከዚያ በኋላ አምቼዎችን አሥመራ ውስጥ ለመለየት ቀላል ነበር። አማርኛ የሚናገሩ፣ በአረማመዳቸው፣ በአለባበሳቸው፣ በአንጻራዊ መልኩ በተላበሱት ግላዊ ነጻነት ይታወቃሉ። የአማርኛ ሙዚቃ በአሥመራ እንግዳ በኾነ መልኩ በስፋት የሚያዳምጡትም አምቼዎች ነበሩ።

“አምቼ” መባል የመገለል ስሜት የሚፈጥርባቸው እንዳሉ ሁሉ ብዙዎች እንደማንነታቸው መገለጫ ይጠቀሙበታል። እንዲያውም የኩራት ምንጭ አርገው የሚወስዱትም አሉ። ኢየሩሳሌም ኀይሌ የከፈተችው “አምቼነቴን እወደዋለሁ” የሚለው አምቼዎች እየተገናኙ የሚጨዋወቱበት በየቀኑ አባላቱን እያበዛ ነው። በመላው ዓለም የተበተኑ አምቼዎች እየተገናኙ  ስለገጠማቸው እና ስለኾነባቸው ነገር ሁሉ የሚወያዩበት ገጽ ነው።

“አምቼ”ዎች በቁጥር ምን ያህል እንደኾኑ የተጨበጠ ወይም በጥናት የተደገፈ ማስረጃ ባይኖርም በስያሜው የሚጠሩ አንዳንዶች ግን “አምቼ”ን እንደ የኤርትራ 10ኛው ብሔር አድርገው ይቆጠሩታል። የ“አምቼ”ዎች ትክክለኛ አኀዝ ባይታወቅም ከጦርነቱ በኋላ ከኢትዮጵያ የተባረሩ ኤርትራውያኖች ቁጥር 75ሺሕ እንደሚደርስ ኦፌሲሊያዊ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ማነው የተባረረው?

ይፋዊ መረጃዎች በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት የተባረሩ ትውልደ ኤርትራውያን መካከል አብዛኛዎቹ ረዥሙን የሕይወት ዘመናቸውን በኢትዮጵያ የተወለዱ እና ያሳለፉ ናቸው።  በ1990 ዓ.ም ወደ ኤርትራ በመጀመሪያ ዙር በተባረሩ ላይ በተደረገ ሰርቬይ 59 በመቶ የሚኾኑት ከ25 እስከ 60 ዓመት የሚኾነውን ጊዜያቸውን ያሳለፉት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው። ሁሉም በሚባል መልኩ የኢትዮጵያ ዜግነት ያላቸው ሲኾኑ ብዙዎቹም በኤርትራ ሕዝበ ውሳኔ ያልተሳተፉ ነበሩ።

በ1985 ዓ.ም በተደረገው የሕዝበ ውሳኔ ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ ከነበሩ እና ድምፅ ለመስጠት ከተመዘገቡ 57,710 ትውልደ ኤርትራውያን መካከል 99.5 በመቶ የሚኾኑት ነጻነትን የመረጡ ሲኾን 204 ሰዎች ብቻ ከኢትዮጵያ ጋራ መኖርን መርጠዋል። ከአምስት ዓመት በኋላ የኢትዮጵያ መንግሥት ለ“አገር ደኅንነት ስጋት ናቸው” በሚል ብዛት ያላቸውን ትውልደ ኤርትራውያን ከኢትዮጵያ አስወጥቷል። ብዙዎቹ ትውልደ ኤርትራውያንን ከአገር እንዲወጡ የተደረገው ህግሐኤ (ህግደፍ)ን በገንዘብ በመደገፍ እና ትሥሥር በመፍጠር ተወንጅለው ነበር። በቀጣዩ ዓመት 1991 ዓ.ም በሳምንት ቢያንስ እስከ 1500 ዜጎች ከኢትዮጵያ ሲባረሩ ነበር።

አብዛኛዎቹ ተባራሪዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የሥራ መስኮች ተሠማርተው የነበሩ ናቸው። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አጣሪ ልዑክ ቁጥራቸው 250 በሚደርስ የትውልደ ኤርትራውያን ቡድን ላይ ባደረገው ማጣራት መምህራን፣ የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኞች፣ ሜካኒኮች፣ ነጋዴዎች እና የዩኒቨርስቲ መምህራንም ጭምር ከተባራሪዎቹ ውስጥ ተካተው ነበር። ከዚህ ቡድን ውስጥ አንድ የሕክምና ባለሞያ እና ሁለት መነኩሴዎችም ነበሩበት። አብዛኛዎቹ ዕድሜያቸው ከ60 በላይ የነበረ ሲኾን ኤርትራን ረግጠው የማያውቁ  እና ትግርኛ ቋንቋ የማይናገሩ ነበሩ።(Case Material on Ethnic Eritrean Deportees from Ethiopia Concerning Human Rights Violations The Uprooted :  Case Material on Ethnic Eritrean Deportees from Ethiopia  Concerning Human Rights Violations  by Prof. Asmarom Legesse  on behalf of Citizens for Peace in Eritrea) ተባራሪዎቹ ወደ ኤርትራ የሚወሰዱት በአራት የድንበር አቅጣጫዎች ነበር። ብዙዎቹ ወደ አሥመራ የገቡት በኦምሃጀር- ተሠነይ- አሥመራ ሲኾን፣ የተወሰኑ በቀይ መስቀል ተባባሪነት በአሰብ በኩል ወደ ኤርትራ ተሸኝተዋል። ጥቂቶች የጦርነቱ ግንባር በነበረችው ዛላምበሳ እና መረብ ዓዲዃላ በኩል ወደ አሥመራ ተጉዘዋል። ሌሎች ደግሞ ወደ ኤርትራ ሳይኾን ወደ ኢትዮጵያ የጠረፍ ከተሞች ሞያሌ እና ጅቡቲ ተወስደው ከአገር እንዲወጡ ተደርገዋል።  ይህ ብዛት ያላቸውን ዜጎች ከአገር የማስወጣት ተግባር በሁለቱም የፖለቲካ ኀይሎች እንደሞያ የተያዘ ይመስላል። በ1983 ዓ.ም ብዛት ያላቸውን ኢትዮጵያውያንን  ሕግሐኤ ከኤርትራ ሲያስወጣ በወቅቱ የኢህአዴግ መንግሥት ስለ ተፈናቃዮቹ ምንም ዓይነት እውቅና ለመስጠት ፈቃደኛ አልነበረም።  ከ1990 ዓ.ም የደንበር ጦርነቱ መጀመር በኋላም የኤርትራ መንግሥትም “ኢትዮጵያዊ” ያላቸውን ዜጎችበምላሹ ከሀገር አባርሯል።

ከካምፓላ 73 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ጂንጃ ከተማ የሚኖሩ እና በወቅቱ ወደ ኤርትራ የገቡትን ዜጎች በመቀበል ሂደቱ ላይ  ተሳታፊ የነበሩ አንድ ውስጥ አዋቂ ተባራሪዎቹ ወደ አሥመራ ሲገቡ የነበረውን ስሜት ለአዲስ ነገር እንዲህ ሲሉ ያብራራሉ፦  “የመጀመሪያውን ዙር ተባራሪዎች ስንቀበል የነበረው ከፍተኛ የቁጭት ስሜት ነበር። በከፍተኛ ስሜትም ነበር። የመጀመሪያዎቹ ተፈናቃዮች አሥመራ ዩኒቨርስቲ እንዲያርፉ ተደረገ፤ ዘመድ ያላቸው በየዘመዶቻቸው እንዲሄዱ ተደረገ። በብዙዎቹ ተባራሪዎች ላይ የላቀ ቁጭት እና ግራ መጋባት ይታይ ነበር።” ይላሉ።

“ሙሉ ቤት እና ሀብት የነበራቸው አባዎራዎች ብርድ ልብስ እና አንሶላ ለመቀበል ሲሰለፉ ለብዙዎቹ አንገት የሚያስደፋ ነበር። እስካሁን ድረስ ያልሻረ ጠባሳ ነው” ሲሉ የተፈጠረውን ችግር ያስረዳሉ። የችግሩ መጠን የተባባሰው ደግሞ የተባራሪዎች ቁጥር በየቀኑ እየናረ ሲመጣ እና የአሥመራ አቅም ከሚችለው በላይ ሲኾን ነበር። ያውም ብዙዎች ከመላው የቤተሰባቸው አባላት ጋራ የመምጣት ዕድል ባለገኙበት ኹኔታ።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሕፃናት ፈንድ (ዩኒሴፍ) በሁለት የተባራሪዎች መቀበያ ጣቢያ ባደረገው ሰርቬይ በሰኔ 1990 ወደ ኤርትራ ከተባረሩት ውስጥ 63 በመቶ የሚኾኑት አዋቂ መላሾች ከልጆቻቸው ተለያይተው እንደመጡ ተናግረዋል። ብዙዎቹም ሀብት እና ንብረታቸውን በወጉ ለማደራጀት እንኳ ዕድል አልነበራቸውም። ይህን መሰሉ ትውልደ  ኤርትራውያንን ሰብአዊነት በጎደለው መልኩ ከኢትዮጵያ የማስወጣቱ ሂደት በወቅቱ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ዓለም አቀፍ ነቀፋ ያሰነዘረ ነበር። ነቀፋው እና ትችቱ በወቅቱ በነበረው ኹኔታ ላይ ብቻ የተወሰነ እና ተባራሪዎች ከዓመታት በኋላ ሊገጥማቸው የሚችለውን የማኅበራዊ ኑሮ ቀውስ ከግምት ውስጥ የከተተ አልነበረም።

ይህ ሁሉ ታሪክ ከተፈጸመ ከዐሥር ዓመት በኋላ ያለው የተባራሪዎች በተለይም የ“አምቼ”ዎች ሕይወት በምስቅልቅል ኹኔታዎች የተሞላ ነው። ለአዲስ ነገር ታሪካቸውን ያጋሩ “አምቼ”ዎችም ይህንኑ እውነታ ይቀበሉታል። ለደኅንነት በመስጋት ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁት ኹኔታውን በቅርበት ሲከታተሉ የነበሩ የጂንጃው ውስጥ አዋቂም ወደ ኤርትራ የገቡት አምቼዎች የተለያዩ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሥነ ልቡናዊ  ችግሮችን መጋፈጣቸውን ይመሰክራሉ።

የአምቼነት  ዕዳ

እንደ ማኅደረ ያሉ ብዛት ያላቸው የትውልደ ኤርትራውያን ልጆች እና ወጣቶች አሥመራን ካጥለቀለቁ በኋላ ያጋጠማቸው ያልጠበቁት እና ካደጉበት በብዙ የሚራራቅ ነበር። ብዙዎቹ  አሥመራን እና ነዋሪዎቿን ሲያስተውሉ እጅግ ወግ አጥባቂ እና የውጭ ሰው እና አስተሳሰብ በቀላሉ የማያስገባ ዝግ ኾነው አገኙት። እነርሱ ካላቸው አንጻራዊ የኾነ “ተራማጅ” ማኅበራዊ መስተጋብር አንጻር ከአሥመራ ነባር ነዋሪዎች ጋራ መዋሃድ እጅግ ፈታኝ ነበር። የሚናገሩት ቋንቋ አማርኛ በመኾኑ አምቼዎች ሙሉ በሙሉ ከአሥመራ ነዋሪዎች ጋራ እንዳይዋሃዱ አርጓቸዋል።

“በአረማመድ ሳይቀር ማን አምቼ እንደኾነ ትለያለህ” ይላል ቢኒያም። “አምቼ”ዎች በሚሰሙት ሙዚቃም ተነጠለው ይታወቃሉ። የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጫፍ በደረሰበት ሰሞን እንኳን በአሥመራ እንዲሁም ከረንን በመሰሉ አነስተኛ ከተሞች ውስጥ በሚገኙ ትናንሽ የመዝናኛ ቤቶች ውስጥ ሳይቀር የአማርኛ ሙዚቃ እንደልብ ማጫወታቸው በጤና አልታየም። ይህንን ተከትሎም የአማርኛ ሙዚቃዎችን በየምሽት ክበቦች ማጫወት እንዲቀር ታግዷል።

“ከመባረሩ ሂደት ጋራ በተያያዘ ብዙዎቹ የሥነ ልቡና ተጽዕኖ ውስጥ ነበሩ።” ይላል ቢኒያም። ማንነታቸው ሁለት ቦታ የተሰፋ ነው። አዲስ አበባ እና አሥመራ። ማኅደረም ከዚህ አልወጣም።  ከአደገበት ቀዬ ተነቅሎ ያለ ውዴታ እና ፈቃዱ፤ በሚያዋርድ እና የሰውነት ክብርን በሚነካ መልኩ ወደ ኤርትራ መላኩ ያብሰለስለዋል። ዛሬ ልቡ ለኤርትራዊነት ያጋድላል። ግን ኤርትራዊ በመባልም ምሉዕነት አይሰማውም።  “የጓደኞቼ ፍቅር እና ወዳጅነታቸው ለአፍታ ባይጓደልብኝም ስያሜዋ(”አምቼ” )  አንዳች ክፍተት በልቤ ውስጥ ፈጠረች። ኤርትራንም እንደ ኢትዮጵያ ጊዜያዊ መጠለያዬ እንጂ ቋሚ አገሬ ለማለት የማልደፍራት እንደኾነች ገባኝ። ኢትዮጵያዊ ነኝ እንዳልል መባረሬ መልሱን ሰጥቶኛል” ሲል የተፈጠረበትን ግራ መጋባት ያስረዳል። “የማልክደው ነገር ከኢትዮጵያ በመባረሬ ለኤርትራ ያለኝን ፍቅር መጨመሩ ነው።”

ማኅደረ ያንን ጊዜ የሕይወቱ “አስጨናቂ” እና “አስቸጋሪ” ወቅት አድርጎ ይቆጥረዋል። ከሁሉ ፈተና የኾነበት ገቢ ማግኘት አለመቻሉ ነበር። የአባቱ ዘመዶች የመረዳዳት ጠንካራ ባህል ታክሎበት እንኳ ኑሮን መግፋት እንደ አለት ጠጥሮበት ነበር፡፡ ተንቀሳቅሶ ለመሥራትም የሚያስችል ምንም ዐይነት ቀዳዳ አልነበረም።

ለአብዛኛዎቹ “አምቼ”ዎችም ሕይወት እንዲያ ነበረች። ከብሔራዊ አገልግሎት ከተረፉ አሥመራ ውስጥ አለ የተባለውን ማንኛውንም ሥራ በመሥራት ይታወቃሉ። በብዙ የአሥመራ ነዋሪዎች የማይደፈሩ እንደማስተናገድ ያሉ ሥራዎችን ሳይቀር ይሠራሉ። አንዳንድ እንስቶችም ተገደው ወደ ሴተኛ አዳሪነት ገብተዋል። አንዳንዶችም በአሥመራ ባልተለመደ ኹኔታ ለአደገው ዝርፊያ ተጠያቂ የተደረጉት እነርሱው ናቸው።  “ሌብነት፣ ማታለል እና በቡድን መደባደብ ከአምቼዎች ጋራ ብቻ እየተያያዘ የሚነሳ ነገር ኾኖ ነበር” ይላል መኖሪያውን ናይሮቢ ያደረገው በፀጋ ሳህለ። ይህ ተደራራቢ ከመጥፎ ነገሮች ጋራ የመዛመድ ችግር የገጠማቸው አምቼዎች የመገለል እና የራሳቸውን ክበብ በመሥራት መራቅን እንዲመርጡ አድርጓቸዋል።

የኤርትራ መንግሥት የሚከተለው ዜጎችን በወታደራዊ አመለካከት የመቅረጽ ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ ለአምቼዎች የሚመች አልኾነም። የኤርትራ መንግሥት መሪዎች አክራሪ የኤርትራዊ ብሔርተኝነት አቀንቃኞች ናቸው። ይህ የአምቼ ማንነት ከተገነባበት መሠረት ጋራ የሚፋለስ ነው። የአምቼዎች ብሔራዊ ማንነት በኢትዮጵያም በኤርትራም ፖለቲከኞች እና ልሂቃን ዘንድ  እውቅናም ገና አልተሰጠውም።  አምቼዎች ማንነታቸው የተገነባው በሁለት ጠንካራ ብሔርተኛነትን በሚያቀነቅኑ (ኢትዮጵያ እና ኤርትራ) ወገኖች መካከል ነው። ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነትም ኾነ የኤርትራ ብሔርተኝነት አንዱ ለአንዱ እውቅና የሚሰጡ አይደሉም። ተፎካካሪ ናቸው።  የሁለቱም ብሔርተኝነት አቀንቀኞች “ቀናተኞች” ናቸው። አንደኛው ሌላውን አይቀበልም። አሥመራ የሚናኘው የብሔርተኝነት አመለካከት “ለ30 ዓመት ከኢትዮጵያ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት በተደረገውን ጦርነት እና ድል “ ውስጥ የበቀለ እና ያደገ ነው። የኢትዮጵያ ብሔርተኝነትም ለኤርትራ ብሔርተኝነት እውቅና የሚሰጥ ሳይኾን እንደ ስኅትት እና ክህደት ይቆጥረዋል። የአምቼዎች ማንነት የተገነባው ደግሞ የአንዱን የብሔርተኝንት እንቅስቃሴ በመናድ እና የሌላኛውን በመደገፍ ሳይኾን በሁለቱ የብሔርተኝነት አጽናፎች መካከል ያለውን መካከለኛ ቦታ ይመርጣል። አምቼዎች ማንነታቸውን የሚገልጹት በሁለቱ ብሔራዊ “ቤቶቻቸው” ነው። ሁለቱንም እንደቤታቸው ያያሉ። ብዙዎቹ ከሁለቱም ቤቶቻቸው ርቀዋል።  ነገር ግን ደግሞ  ከሌላኛዋ “ቤታቸው” ኢትዮጵያ በግድ የተነቀሉም ናቸው።

አዲስ አበባ

አምቼዎች ኑሮ በአሥመራ እጅግ ፈታኝ ኾኖባቸዋል። ኢኮኖሚው እና ማኅበራዊው ችግርም ቶሎ ሊቀረፍ ያልቻለ ነበር። ብዙዎቹ ከድንበር ጦርነቱ በኋላም አሁንም ብሔራዊ አገልግሎት ከመስጠት አልወጡም። መቼ እንደሚወጡም አቶ ኢሳያስ አፈወርቂ እና እግዜር ብቻ የሚያውቁ ይመስላል። አሥመራ ላይ ያለው የአቶ ኢሳያስ አስተዳደር በየጊዜው ፍፁም አምባገነንነቱን እያጠናከረ መሄዱ የአምቼዎችን ሕይወት መፈናፈኛ እንዳይኖረው አድርጎታል። እንደ ማኅደረ ያሉት ግን ተሳክቶላቸው አገራቸውን ጥለው ዳግም ስደት ገብተዋል።

ዳግም ስደት……ዘጸአት ለአምቼ?

አሥመራም ያልተመቻቸው ብዙ “አምቼዎች” ኤርትራን ለመልቀቅ ድንበር ማቋረጥ ጀመሩ። መጀመሪያ ወደ የመን፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን። ለደላሎች ብዙ መክፈል ግድ ይላል። ገንዘብ ያላቸው ብቻ ለቀናት የእግር ጉዞ በማድረግ ከኤርትራ ደንበር ጠባቂዎች ተደብቀው ወደ ከሰላ (ሱዳን) በሕገ-ወጥ መንገድ ለመውጣት ይሞክራሉ። የተሠነይ-ከሰላ መንገዱ አንዱ ሲኾን ከኤርትራ ለመውጣት እስከ 4ሺሕ ዶላር የሚቀበሉት አስተላላፊዎች ሌሎችም በሮች አሏቸው። የቻሉ ይወጣሉ፤ ሌሎች ደግሞ ተይዘው ይታሠራሉ ወይም ይገደላሉ።

በዚህ መልክ ኤርትራን ለቀው ከተሰደዱት መካከል አንዱ ቢኒያም ነበር። እርሱ እንደ አብዛኛዎቹ አምቼዎች በድንበር ግጭት በተነሳው ጦርነት ምክንያት ራሱን አሥመራ ላይ አላገኘውም። በ1983 ዓ.ም ደርግ ሲወድቅ ወደ ኤርትራ ሄደ። ከአዲስ አበባ አስመራ በአውቶብስ እየተመላለሰ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን፣ ሲጋራ እና ማስቲካ ይነግድ የነበረው ቢኒያም የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲነሳ አሥመራ ላይ ነበር፤ ድንበርም ተዘጋ። ብዙዎችም ተባረሩ። ያኔ አሥመራ ላይ መቅረት ግድ ኾነ።

ባለትዳር እና የሁለት ልጆች አባት የነበረው ቢኒያም ንግዱን ቢቀጥልም ከአንድ አስቸጋሪ ነገር ጋር ተፋጠጠ። እንደ ደንቡ የብሔራዊ አገልግሎት ግዴታውን መወጣት ነበረበት። በኤርትራ መንግሥት ሕግ መሠረት ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 40 ዓመት የኾናቸው ዜጎች የብሔራዊ አገልግሎት የመስጠት ግዴታ አለባቸው። ሦስተኛ ልጁን እርጉዝ የነበረችውን ባለቤቱን ጥሎ ላለመሄድ ያልፈለገው ቢኒያም ከባለሥልጣናቱ ጋራ ድብብቆሽ ጀመረ። ቁጥጥሩ ጥብቅ እየኾነ ሲመጣ የቀረው ሁለት አማራጭ ነበር።  ወደ ብሔራዊ አገልግሎት መሄድ ወይም ከሀገር መውጣት።

አገር ጥሎ መውጣት ግን ቀላል አልነበረም። በየቦታው ያሉትን ኬላዎች ማለፍ፣ በአልሞ ተኳሽ ወታደሮች የሚጠበቅ ድንበርን ማለፍ ይጠይቅ ራሱን የቻለ ፈተና ነበር። ከአሥመራ ተሰነይ በአውቶብስ የተጓዘው ቢኒያም ድንበር አቋርጦ ከሰላ ለመግባት የ17 ሰዓት የእግር ጉዞ መሄድ ግድ ኾኖበታል። “እኛ የወጣንበት መንገድ አሪፍ ነበር” ይላል ቢኒያም። የወታደሮች አፈሙዝ የሌለበት፤ ይህን መንገድ የሚያውቁ ሰዎች ግን በወቅቱ “ጫን ያለ” ክፍያ ነበር የሚጠይቁት።

የተጠየቀውን 1500 ዶላር ከፍሎ የሱዳን የድንበር ከተማ የኾነችው ከሰላ የደረሰው ቢኒያም በድንበር ጠባቂ ፖሊሶች እጅ ላይ ይወድቃል። “ከሰላ ስገባ ጀለቢያ አድርጌ ነበር። ጸጉረ ልውጥ ስለኾንኹ በፖሊሶች ተያዝኩ። በኪሴ 3000 ዩሮ እና 200 ዶላር ነበረ። ፖሊሶቹ ራቁቴን አድርገው ፈተሹኝ” ይላል። የኮሎኔል ማዕረግ ካለው ፖሊስ ፊትም እንዲቀርብ ተደረገ። “የሚያውቁት ገንዘብ ዶላር ስለነበር የያዝኩትን 200 ዶላር ሰጠኋቸው። ዩሮውን ስላላወቁት ለቀቁኝ” ሲል እንዴት ለመቋቋሚያ ብሎ የያዘው ገንዘብ እንደተረፈለት ይናገራል። ዛሬ ራሱን ጁባ ከማግኘቱ በፊት ከአገር አገር ዞሯል። ካርቱም- አዲስ አበባ- ናይሮቢ-ሉዋንዳ -ካምፓላ።

አሁን ኬንያ የሚገኘው ማኅደረ ድንበር ከመሻገሩ በፊት ኤርትራውያንን እና አምቼዎችን ማስኮብለል ሥራው ነበር። ከባድ የኾነበትን የአሥመራ ኑሮውን ትንሽ መልክ ያስያዘው ይኼው ሥራው ነበር። ወደዚህ ሥራው ደግሞ ያመጣው የ“ኮምቢሽታቶው ጮሌ” ሚካኤል ነበር። ሚካኤል የአባ ሻወል ሠፈር ልጅ ነው። ነገር ግን ውሎው እና ተግባሩ ኮምቢሽታቶ በመኾኑ ነበር  ሚካኤል ኮምቢሽታቶ የሚል ስያሜ ያገኘው። በጣም ተግባቢ  ነው።

ሚካኤል እና ማኅደረ የተግባቡት የ“ኮምቢሽታቶው ጮሌ” ማኅደረ ዘወትር ከማይጠፋባት “በረኸት ሻይ ቤት” በትዝታ ሲናውዝ ያገኘው ቀን ነበር። “አንቺ አምቼ አሁንም ሠፈር አልለመድሽም ?” አለው ማኅደረን! በቀላሉ ተግባቡ። ወዳጅነታቸው ጠነከረ። ሳምንቱን ሙሉ አይነጣጠሉም። ውሏቸው “ካምቦሎ”፣ “ትራቮሎ”፣ “ፊያት”፣ “ሳንፍራቼስኮ”፣ “አክሪያ” እና ሌሎች ሠፈሮች ኾነ። ማኅደረ አዲስ አባባ እያለ ወደ ሲኒማ ኢትዮጵያም ኾነ ሲኒማ አምባሳደር ብቅ የማለት ልምድ አልነበረውም። በአሥመራ ግን ደንበኛ ኾነ። በ“ሲኒማ አዝመሪኖ” እና በ“ሲኒማ ካፒታል” በየቀኑ ይታደማል። ሚካኤል ይከፍላል፤  ማኅደረ ይዝናናል።

አንድ ቀን የአሥመራ መለያ  የኾነው ካቴድራል ወደ ሚገኝበት  ኮምቢሽታቶ ተያይዘው ነጎዱ። አምባሳደር ሆቴል እዚሁ አቅራቢያ ይገኛል። በአቅራቢያው ወደሚገኝ  ባለ አንድ ፎቅ ወዳለው ቤት ተያይዘው ሄዱ።  “ፈጠን ብለህ ግባ” አለው ሚካኤል ኋላ እና ፊቱን እየተገላመጠ። “የሕንጻውን ዋና በር እንዳለፍኩ ግድግዳ ተደገፌ ጠበቅኹት። ‘ተከተለኝ’ የሚል ትዕዛዝ ብቻ ሰጥቶኝ ነጠር ነጠር እያለ ከፊት ለፊቴ ይመራኝ ጀመር” ይላል ማኅደረ ።

የገቡት ከሕንጻው ጀርባ ካለች አነስተኛ ክፍል ነበር። ሦስት ወጣቶች አትነጋገሩ የተባሉ ይመስል በፀጥታ ተቀምጠዋል። ሚካኤል ንግግር አላበዛም። “በማለዳ ተነስታችሁ እዚሁ እንገናኛለን፤ ቻው” የሚል ቃል እንደተናገረ አንደኛው ወጣት ለሚካኤል በእጁ አንድ ነገር አስጨበጠው። “ተረጋግታችሁ ውጡ” የሚል ትዕዛዝ ብቻ ሰጥቶ በጥንቃቄ ሕንጻውን ለቀቀው ወጡ። የኮምቢሽታቶውን ጮሌ ዋነኛ የገቢ ምንጩ በድብቅ ከኤርትራ የሚወጡ ዜጎች “መርዳት” መኾኑን ማኅደረ ያወቀው በዚያ አጋጣሚ ነበር።

አሥመራ ከተማ

የኮምቢሽታቶው ጮሌ ዋና ሥራ ተጓዦቹ ከአሥመራ እንዲወጡ መርዳት ነው፤ ከዚያ በሻገር ስላለው ደግሞ ሌሎች ባልደረቦቹ ይጨነቁበታል። ከተሳካ እስከ ኢትዮጵያ ወይም ሱዳን ድንበር ያደርሳሉ። ከዚያ በኋላ ያለው ጣጣ የስደተኛው ይኾናል። በወቅቱ በርካቶች በውትድርናው ሥራ የመረራቸው፣ ሳዋን የሚሸሹ እና የተሻለ ኑሮ የሚፈልጉ ወጣቶች ነበሩ። ውቧ ግን ሕይወት አልባዋ አሥመራም ሰልችታቸው ነበር። ለእርሱ ብቻ ሳይሆን ለብዙ አምቼዎች። የመንግሥት ቁጥጥር ከፍተኛ በመኾኑ ዜጎችን ማስኮብለል ቀላል ሥራ አልነበረም። እጅግ ጥንቃቄን የሚሻ ነው። ከሞት ጋራ አንገት ለአንገት ተናንቆ የሚሠራ ነው።

ከቀናት ምክክር እና ልምምድ በኋላ ማኅደረ የሚካኤል ረዳት ኾነ። የተሰጠው ሚና ደግሞ ከኢትዮጵያ የተባረሩ እና መመለስን የሚሹ አምቼዎችን ማገናኘት ነበር። ሥራው  መልካም ነበር፤ ገቢ አለው። ነገር ግን ሕይወት ከወዲህ ወዲያ የሚያላጋቸውን ለጋ ወጣቶች አደጋ ባለው ጉዞ ማሾለክ ለህሊናው  ፈታኝ ኾኖበታል። ግን ሕይወት ሌላ የተሻለ ምርጫ አልሰጠችውም። “አስገራሚው ነገር በየቀኑ ከሁለት ያለነሰ ሰው ለመኮብለል እንደሚፈልግ ማወቄ ነበር። አገር የሚሰደድ ነው የሚመስለው። እንደዚህ ጥብቅ የመንግሥት ቁጥጥርም እያለ የሚኮበልል ሰው ማግኘት ሳይኾን እንዴት ለማስኮብለል እንደሚቻል ነው የሚቸግረው” ይላል።

ማኅደረ በመጨረሻ ራሱን ለዳግም ስደት አጨው። አሥመራ ቢቆይ ከአባ ሻውል እስከ ኮምቢሽታቶ…እንደ ልብ ወዲህ ወዲያ ሲል እንደማይኖር ያውቀዋል። ሳዋ አፉን ከፍቶ ይጠብቀዋል። “በአዝመሪኖ ያለው ቆይታዬም በሳዋ ግዞት መጠናቀቁ ስለማየቀር ከወዲሁ ልኮብልል ስል ራሴን መከርኩት” ይላል ውሳኔ ላይ ስለደረሰበት ወቅት እና ኹኔታ ሲያብራራ። ለስደት የመረጠው መንገድ ግን ሌላ ፈተና ይዞ መጣ። ኢትዮጵያን እንደ መሸጋገሪያ ድልድይነት ቢወስዳትም የኤርትራን ድንበር አልፎ ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ የማንነት ጥያቄው አፍጥጦ መጣበት “እኔ የማን ነኝ?” የሚል።

“አሥመራን እስከምለቅ በስጋት ውስጥ ጥያቄውን አዳፈኜው የነበረ ቢኾንም አክሱም ከተማ ስደርስ ዐይኑን አፍጥጦ መጣብኝ” ይላል።  ከማኅደረ ጋራ አብረው የኮበለሉት ወደ ሽመልባ መጠለያ ካምፕ ሲገቡ እርሱ ግን ወደ አዲስ አበባ ተጓዘ። አዲስ አበባ ጥቂት ከሰነበተ በኋላ ወደ ኬኒያ አቀና። ብዛት ያላቸው አምቼዎችም የማኅደረን መንገድ ተከትለዋል።

ሥርጭት በምሥራቅ አፍሪካ

አምቼዎች ከአዲስ አበባ እና አሥመራ ውጭ በመላው የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ተበትነዋል። በተለይ በምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ካርቱም፣ ጁባ፣ ካምፓላ፣ ናይሮቢ፣ ሞምባሳ፣….እና በመላው ዓለም ይገኛሉ። ምሥራቅ አፍሪካ ላይ ደግሞ በብዛት ይገኛሉ። በተለይ  ጁባ እና ናይሮቢ።

ናይሮቢን ከሞይ ጎዳና ዳር ቆሞ ለሚመለከት በግልጽ በሚታይ ኹኔታ ከተማዋ በሁለት ተከፍላ ትታያለች። ዌስትላንድ (Westland) እና ኢስትላንድ (Eastland) በሚል። ምዕራቡ የከተማዋ ክፍል በአረንጓዴ የተሸፈነ፣ አልፎ አልፎም ጥቅጥቅ ያሉ ደኖች ያሉበት፣ በብዛት ከፍተኛ ገቢ ያላቸው የኬንያ ዜጎች፣ ሕንዶች እና የሌሎች አገራት ዜጎች የመኖሪያ ሥፍራ እና መዝናኛዎች የበዙበት ነው። ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ስደተኞች ከሚኖሩባቸው የኬኒያ መንደሮች መካከል አንዱ የኾነው “ሐርሊንግሃም” በዚሁ ምዕራባዊ የናይሮቢ ክፍል (ዌስትላንድ) ይገኛል።

ወደ “ያያ የንግድ ማዕከል” የሚወስደውን መንገድ ተከትሎ ለሚጓዝ ሁሉ ከዳገቱ ላይ ኾኖ “ሐርሊንግሃም” የሚባለው አካባቢ ይቀበለዋል። የአካባቢው ሰላማዊ መኾን እና ማራኪነት አቅሙ ያላቸውን ሐበሾች የሚስበውን ያህል፣ በሌላ ጎኑ ደግሞ በአነስተኛ ዋጋ በጋራ ለመኖር ለቆረጡ የሐበሻ ስደተኞችም መሰባሰቢያ ስፍራ ነው። ሐርሊንግሃም ለመድኀኒዓለም ቤተክርስቲያን ቅርብ ኾኖ መገኘቱም የበለጠ ተመራጭ አድርጎታል። ዐይንዎን በአካባቢው በማይጠፉት ሐበሾች ላይ ያሳርፉ። ምን አልባት ለናይሮቢ አዲስ ከኾኑ ኤርትራዊ፣ ኢትዮጵያዊ  ከሚለው መለያ በተጨማሪም “አምቼዎችንም” እዚህ ያገኟቸዋል። አብዛኞቹ አምቼዎች በሁለቱ ወገኖች መካከል የመዋለል ስሜት ይሰማቸው እንጂ ወደ ኤርትራዊነት ማጋደላቸው አልቀረም፡፡ በተለይም ግማሽ ኤርትራውያኑ በቂ የሚሉትን ምክንያት ያሰቀምጣሉ፡፡ ለአብዛኞቹ ከኢትዮጰያ ወገን ካሉ ዘመዶቻቸው ይልቅ ከኤርትራ በኩል የሚዛመዱ የመረዳዳት ባህላቸው ጠንካራ መኾን ለዝንባሌያቸው ምክንያት ነው፡፡ በፀጋም ይሄን ሃሳብ ያጠናክራል፡፡ “በስመ ኤርትራዊ እርዳታ ብትጠይቀ የሚነፍግህ የለም፡፡ አገር ቤት ብትሄድ ደግሞ ሰርጉም ሃዘኑም ለብቻህ ስለማትወጣው መደጋገፉ የጠነከረ ነው”

በናይሮቢ ያለው የስደተኞች የአኗኗር ዘይቤም ይሄን የሚያሳይ ነው፡፡ ኤርትራውያኑ (አምቼዎቹን ጨምሮ) በአንድ ስፍራ አጀብ ብለው መኖርን ይመርጣሉ፡፡ ለአንዱ በተላከው የድጎማ ገንዘብ የተቸገረ ወገናቸውን ጭምር ይረዱበታል፡፡ መጠለያ የሌላቸውን በዙር በየቤታቸው ከማስጠለል አንስቶ ወርሃዊ የቤት ኪራይ በመክፈል ጭምር አለኝታነታቸውን ያሳያሉ፡፡

ያያ መድኀኒዓለም- ናይሮቢ

የሐርሊንግሃም ጉዳያችንን ከጨረስን “አምቼዎች” በስፋት ወደሚኖሩበት ወደ ምሥራቃዊው ናይሮቢ እናዝግም፤ ከአምቼው ማኅደረ ጊላይ ጋራ። የናይሮቢ ምሥራቁ ክፍል ከምዕራቡ በተቃራኒው ብዙ ለምለም ነገር የማይታይበት፣ ድህነት የደቆሳቸው መንደሮች በብዛት የሚገኙበት እንዲሁም ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚካሄድባቸውን ሥፍራዎች አካቶ የያዘ ነው። ከ“ኢስሊ” ሌላ “ቻይሮድ” ወደ ሚባለው ሰፈር ቢያቀኑ ብዛት ያለቸውን ሐበሾች ችምችም ባለው መንደር መካከል ያገኟቸዋል። በዚህ ሥፍራ ዳር እና ዳር በአማርኛ የተጻፉ ማስታወቂያዎችን ይመለከታሉ።

ከ“ካተሪና ሎጅ” ፊት ለፊት “አሥመራ ሆቴል” ጎላ ብሎ ይታያል። ኢትዮጵያውንም በብዛት ቢገኙም የኤርትራውያኑን ያህል አይኾኑም። ብዙኀኑ በምግብ ሥራ፣ በችርቻሮ እና በመጠጥ ንግድ ራሳቸውን ያስተዳድራሉ። አካባቢው ከኪስዋሂሊ እና ከእንግሊዝኛ ቋንቋ ይልቅ ትግርኛ እና አማርኛ ጎልተው የሚነገሩበት ነው።

ካሪያኮር እና ፓንጋኒ የሚሉት አካባቢዎች በሐበሻ የሚዘወተሩ ቢኾንም የኤስሊን ያህል ግን ሐበሻን አያስተናግዱም። ኤስሊ የሶማልያውያን የበላይነት እየነገሠ የመጣበት ትልቁ የንግድ ሥፍራ ነው። በብዙ መልኩ ከአዲስ አበባው መርካቶ ጋራ ይቀራረባል። ይኹንና ኤስሊ የሚንቀሳቀሰውን የዶላር መጠን መርካቶ በዓመት ለማንቀሳቀስ አቅም ያለው አይመስልም። በዚህ ወከባ እና ግርግር በበዛበት ሥፍራ ሐበሾችም የራሳቸው ድርሻ አቸው። ሁለተኛ፣ ዘጠነኛ፣ ዐሥረኛ እና ዐሥራ አንደኛ የሚባሉት መንገዶች በብዛት ሐበሾችን የያዙ ክፍሎች ናቸው። ሚሚ ሱቅ፣ ቴዲ ሙዚቃ ቤት፣ የባህል መደብር . . የመሳሰሉት የአማርኛ ማስታወቂያዎች ጎልተው የሚታዩት ግን በተለይ በዘጠነኛ እና በዐሥረኛ መንገዶች ነው።

በናይሮቢ ጉራንጉሮች ውስጥ የእሱን መሰል ታሪክ ያላቸው አሚቼዎች ጉዞ ገታ ያድርጉ እና ወደ ደቡብ ሱዳን ዋና ከተማ ጁባ ይጓዙ። ከናይል ወንዝ አቅራቢያ ከተሠራው እና የጁባ ዐይን ከኾነው “ብሪጅ” ሆቴል ተነስተው ጉዞዎን ቢያደርጉ እዚህም እዚያም ሐበሾችን ይመለከታሉ። “ኮኞ ኮኞ”፣ “ገበል ኩጁ”፣ “ኒው እና ኦልድ ከስተመስ”..እንዲሁም በመላዋ ጁባ ቢዘዋወሩ እንደልብ የሚያገኙት እነርሱኑ ነው። ጁባ ሮድ በሚገኘው “ኩሽ ሆቴል” ገብተው ዐይንዎን ጣል ቢያደርጉ እዚህም እዚያም ሐበሾች ክብ ሠርተው ሲያወጉ ስልክ ሲደውሉ፣ ጥሪ ሲቀበሉ ያያሉ።

ጁባ...ደቡብ ሱዳን

ጁባ የደቡብ ሱዳን ልብ የኾነች የንግድ ከተማ ነች። ወደ ምግብ ቤቶች ጎራ ሲሉ የሚያስተናግዱዎትም አዲስ አባባ የሚያውቋቸው ኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ሊኾኑ ይችላሉ።  ጁባ ነፍስ የምትዘራው በኤርትራውያን እና በኢትዮጵያውያን ነው። ከከፍተኛ የመንግሥት አማካሪዎች እስከ ሾፌር፣ ነጋዴ፣ አስተናጋጅ፣ ወያልነት….ድረስ ጁባ ትዘወራለች። አምቼዎች ከኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን መሳ ለመሳ ኾነው ሕይወታቸውን ይገፋሉ። ቢኒያም እዚህ ይኖራል። ማኅደረ ደግሞ ኬንያ። ብዙዎች “አምቼዎች” እንደ ቢኒያም አሊያም እንደ ማኅደረ ዕድለኞች አልነበሩም። ዛሬ በሕይወት ተርፈው ታሪካቸውን ለማውራት ዕድሉን አላገኙም።

አሳዛኙ ዕጣ

አንዳንዶቹ እጅግ ዘግናኝ በሚባለው የባድመ ጦርነት ከለብ ለብ ሥልጠና በኋላ እንዲሳተፉ ተደርገዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ያባረራቸው ብዛት ያላቸው አምቼዎች አሥመራ በገቡ በስድስት ወር ጊዜ ወስጥ ወደ ሳዋ ወታደራዊ ማሠልጠኛ እንዲሄዱ ይደረጉ ነበር። የሳዋ ስምንተኛ እና ዘጠነኛ ዙር ሠልጣኞች ብዙዎቹ አምቼዎች ናቸው። ሥልጠናውን እንደጨረሱ እጅግ ዘግናኝ እና ለሰው ሕይወት ደንታ ባልነበረው የባደመ ጦርነት ተማገዱ። ብዙዎቹም ሕይወታቸውን እና አካላቸውን አጥተዋል። አሳዛኙ ዕውነታ ደግሞ “አምቼ”ዎች በጦርነቱ ወቅት በሁለቱም ወገኖች የማይታመኑ መኾናቸው ሕይወታቸውን የበለጠ ያከፋው እንደነበር አዲስ ነገር ዩጋንዳ -ጂንጃ ውስጥ ያነጋገራቸው ለጉዳዩን ቅርበት የነበራቸው ግለሰብ ያስረዳሉ። “ጦርነቱ ላይ ስለ ተሳተፉት ወጣት ትውልደ ኤርትራዊ ዜጎችን (አምቼዎችን) አስብ።  በተለይ አንዳንዶቹ ወጣቶቹ ኢትዮጵያዊ ነን ብለው የሚያስቡ፤ ከአዲስ አባባ ውጭ ሌላ ከተማ ዐይተው የማያውቁ ነበሩ” ይላሉ ውስጥ አዋቂው። “በሕይወትህ አስበህ እና ገምተህ በማታውቀው መልኩ ለማታውቀው አገር ወታደር ኾነህ ራስህን ብታገኘው ምን ይሰማኻል? ከእኛ ወዲያ የአበደ አለ?” ሲሉ በወቅቱ የነበረውን ኹኔታ በጥያቄ መልክ ያስቀምጡታል።

ማኅደረ ይህን መሰል ታሪኮችን ኖሯቸዋል። ተረት የሚመስሉት እውነተኛ የትራጄዲ ታሪኮች ቁጥር ስፍር የላቸውም። “ከአዲስ አባባ ወጥቶ የማያውቅ የ18 ዓመት ልጅ ከአባቱ ጋራ ወደ ኤርትራ ተባረረ፤ ለምን እንደተባረረም በቅጡ ያልተረዳ ወጣት። አሥመራ በገባ በስድስት ወሩ ሳዋ ገባ፤ ባድመ ላይ ሞተ። ለምን ሞተ?…” ማኅደረ ይጠይቃል። አባቱ የልጃቸውን ሞት ከሦስት ዓመት በኋላ ሰሙ። ባዶ ሕይወት። የማኅደረ- አምቼ ትዝታዎች፤ በናይሮቢ።

ከ10ኛ ብሔረሰብ ወደ አምቼዎች ዓለም?

“አምቼ”ዎችን አንዳንዶች “ግራ የተጋቡ” ሲሉ ይገልጿቸዋል። የአዲስ ነገር ዘጋቢዎች ይህን ዘገባ ለማጠናቀር በተንቀሳቀሱባቸው የምሥራቅ አፍሪካ የተለያዩ ከተሞች ናይሮቢ፤ ካምፓላ፣ ጁባ፤ ካርቱም፣..እና ሌሎች ትንንሽ ከተሞች ግን “አምቼ”ዎች ያላቸው ማኅበራዊ ፋይዳ አይተዋል። አምቼዎች “ድልድዮች”፣ “ሰላም አስከባሪዎች” የሚሉ ስያሜዎች ያገኙትም በማኅበራዊ መስተጋብር ላይ ባላቸው አበርክቶት ነው። “አምቼ”ዎች የኢትዮጵያን እና የኤርትራን ሕዝቦች የሚያገናኙ፤ በሁለቱም ውስጥ የሚገኘውን ደካማ እና ጠንካራ ጎን የሚረዱ ናቸው። በሁለቱ ሕዝቦች መካከል አንዱ ለአንዱ ያለውን አሉታዊ ግምት ለመፋቅ በአንድ ተመሳሳይ ወቅት ለኤርትራም፤ ለኢትዮጵያም ወግነው የሚከራከሩ ናቸው።

በጁባ፣ ናይሮቢ፣ ካምፓላ፣ በመሳሰሉ የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች በምድር ወገብ ፀሐይዋ ማዘቅዘቅ ስትጀምር ሐበሾች ወደ ከፈቷቸው ቡና ቤቶች እና ባሮች ጎራ በሉ። የአብርሃም አፈወርቂን ሙዚቃ እንደሰማችሁ የቴዎድሮስ ካሳሁንን “ኻብ ዳህላክን” ወዲያው ልታደምጡ ትችላላችኹ። ሌላም ዘፈን …፤ “አዲስ አበባ ቤቴ” የሚለውን ዘፈን  ጭምር ሁሉ። እነዚህን ዘፈኖች ሲሰሙ ያስከፈቱትን የላጋር ቢራ ቶሎ ቶሎ የሚጎነጩ …ሲጋራቸውንም በላይ በላዩ የሚያጨሱ ወጣቶች ልትታዘቡ ትችላላችሁ። በሙዚቃው ውስጥ ሕይወታቸውን እያነበቡ ትላንትን፣ ዛሬን እና ነገን እያሰቡ እንደሚኾን አትጠራጠሩ።

ብዙዎች “አምቼ”ዎች እንዲህ ዐይነት ሙዚቃ ሲያደምጡ በትዝታ እና በቁጭት ወደ አዲስ አበባ በሐሳብ መመለሳቸው አይቀርም። በአንዳንዶች ሕሊና ከዐሥር ዓመት በፊት ያዩዋትን አዲስ አበባ በዐይነ ሕሊናቸው ድቅን ትላለች። “አምቼ”ዎች ላደጉባት አዲስ አበባ ልዩ ፍቅር እና ግምት አላቸው። ከአዲስ አበባ የተነጠሉበት መንገድ ደግሞ አዲስ አበባን በበጎ ብቻ እንዳያስታውሷት አድርጓቸዋል።

ጁባም ኾነ ናይሮቢ፣ ካምፓላም ኾነ ካርቱም ኤርትራውያን እና ኢትዮጵያውያን አብረው የሚታደሙባቸው የምሽት ክበቦች አንዳንድ ጊዜ ጸብ አያጣቸውም። በአንድ ዜማ አብረው ሲደንሱ የነበሩት እና ራሳቸውን “ሀበሻ “ እያሉ የሚጠሩት  ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ከአፍታ ቆይታ በኋላ ሊጣሉ ይችላሉ-እንደ ድንገት። “በሀበሾቹ” መካከል ፀብ ከተነሳ “ሰላም አስከባሪዎች” በገላጋይነት ከተፍ ይላሉ። “ጁባ ላይ አምቼዎች  ‘ሰላም አስከባሪዎች’ ተብለው ይታወቃሉ” ይላል ቢኒያም።

በመላው የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ተበትነው የሚገኙት ከኢትዮጵያውያን እና ከኤርትራውያን ስደተኞች ወገኖቻቸው መሳ ለመሳ የስደት ኑሮቸውን እየገፉ የሚገኙ “አምቼ”ዎች ልክ በመላው ዓለም እንደተበተኑ የስያሜ ተጋሪዎቻቸው ሁሉ እርስ በእርስ ባላቸው ትሥሥር ይታወቃሉ። “I Love being Amiche” በተሰኘው የአምቼዎች ፌስ ቡክ ገጽ ላይ አስተያየቱን የሰጠ አንድ ወጣት እንዲህ ሲል ምኞቱን አስቀመጠ። “አምቼዎች አንድ ላይ የምንኖርበት ዓለም ቢኖረን እንዴት ደስ ባለኝ።”

ሕልማቸው በእነርሱ ምኞት ብቻ እንደማይሳካ ያውቁታል። ሥልጣን ላይ ያሉት የፖለቲካ ቡድኖች ለጥያቄዎቻቸው የሚኾን መልስ ይዘዋል። ጉዳዩን ለማየት የሚያስችል ፍፁም ፈቃደኝነት ባይታይባቸውም። ማኅደረ ግን ለማንነት ጥያቄው መፍትሄ ያለው ይመስላል። “ከኢትዮጵያዊነት እና ኤርትራዊነት በላይ የጨርቆስ እና የአባ ሻወል ልጅ መባል ይበልጥብኛል” ይላል። ብዙ አምቼዎች በሚገናኙበት የፌስ ቡክ ገጽ ላይ ሰለሞን ዘርዐይ የሚባል አባል  ይህችን ግጥም አሰፈረ።

ብለነው ብለነው ካልኾነ ነገሩ

አምቼና ዶላር የትም ነው አገሩ።

ዘገባ-  ሱቢ ዓለሙ፣ ማስረሻ ማሞ

No Responses to “በ“አምቼዎች” ዓለም ውስጥ፡ ፖለቲካ ፣ ማንነት እና ስደት”

  1. WEHA BEWKTUT EMOCHEEEE…..

  2. This news is intended to give the impression to the readers that the rhetoric of economic development is ridiculous.
    Just out of curiosity, has anyone ever seen any positive news about Ethiopia on ANO?

  3. man neber kahun behuala etiban yemibal neger anteyikim yalew_….tiyake milikit ….

Leave a Reply

You must be to post a comment.

በ“አምቼዎች” ዓለም ውስጥ ፦ ፖለቲካ፣ ማንነት እና ስደት

This post is available in: ኸንግሊስህየማኅደረ ጊላይ የለጋነት ዕድሜ እንዲሁ እንደ ዐይን ጥቅሻ እያለፈ ነው። ወደ ኋላ ተመልሶ ሲያስብ ደስ የሚል ነገር ትዝ አይለውም።ሕይወት ልክ ከማለዳ ጣፋጭ እንቅልፍ እንደሚያባንኑት አስፈሪ የልጅነት የተረት ጭራቆች የተሞላች ትመስለዋለች::  ተረት የሚመስሉ ታሪኮችን እየኖረ፣ እየሰማ እና እየታዘበ እዚህ ደርሷል። መባረር፣ ስደት፣ ሞት… እና በትዝታ መዋትት በሕይወቱ ውስጥ እስካሁንም ይገለባበጣሉ። ሰሞኑን [...]

Nairobi

This post is available in: ኸንግሊስህ

የማኅደረ ጊላይ የለጋነት ዕድሜ እንዲሁ እንደ ዐይን ጥቅሻ እያለፈ ነው። ወደ ኋላ ተመልሶ ሲያስብ ደስ የሚል ነገር ትዝ አይለውም።ሕይወት ልክ ከማለዳ ጣፋጭ እንቅልፍ እንደሚያባንኑት አስፈሪ የልጅነት የተረት ጭራቆች የተሞላች ትመስለዋለች::  ተረት የሚመስሉ ታሪኮችን እየኖረ፣ እየሰማ እና እየታዘበ እዚህ ደርሷል። መባረር፣ ስደት፣ ሞት… እና በትዝታ መዋትት በሕይወቱ ውስጥ እስካሁንም ይገለባበጣሉ።

ሰሞኑን ከናይሮቢ 500 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የካኩማ ስደተኞች ካምፕ ኬኒያ መናገሻ ከተማ ብቅ ብሏል። ለእርሱ ጉዞ አዲስ አይደለም፤ ስንቱን ተጉዟል። ገና የዐሥራዎቹን አጋማሽ በቅጡ ሳይደፍን ከተወለደባት እና አፈር ፈጭቶ ካደገባት አዲስ አበባ እስከ አሥመራ ያለውን የ1176 ኪሎ ሜትር አይረሴ ጉዞ አድርጓል። ጉዞው ግን እንደዚህኛው በፍቃዱ የተደረገ አልነበረም። ያልተጠበቀ እና በስሜት ምስቅልቅል የተሞላ ነበር።  ደም አፋሳሹ እና ትርጉም የለሹ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲነሳ ከኢትዮጵያ ተባርሮ አሥመራ ገባ።

“ኤርትራዊ” በመኾናቸው ምክንያት የመባረር ዕጣ እንደገጠማቸው የስሚ ስሚ ቢሰማም ለጋ ዕድሜው ከአባቱ ጋራ የተባረረበትን ምክንያት በቅጡ እንዳይረዳው አድርጎት ነበር። “እኔ በወቅቱ እንኳን በሩቅ የማውቃትን ኤርትራን ቀርቶ ተወልጄ ያደግኩባትን ኢትዮጵያዊ ዜግነት ምን እንደሚመስል የማሰላስልበት ብስለት ላይ አልደረስኩም። ከትልቁ የዜግነት ጉዳይ ይልቅ የሠፈር ልጅነት ለእኔ ትርጉም ነበረው” ሲል ወደ ኋላ ተመልሶ ያስታውሳል። “‘የጨርቆስ ልጅ’ መባል ያኮራ ነበር” ይላል ማኅደረ የልጅነት ጣፋጭ ጊዜውን ያሳለፈበትን ሰፈር እያሰበ። “የጨርቆስ ልጅነቴን የምገልጸውን ያህል እንኳ ዜግነት የሚባለው ነገር ሳይገባኝ ነው አሻግረው አባ ሻውል የወረወሩኝ።”

ለማኅደረ የአዲስ አበባው ጨርቆስ እና የአሥመራው አባ ሻውል የሚመሳሰሉበት ነገር እንዳላቸው ታይቶታል። ሁለቱ ሰፈሮች ስማቸው ከድህነት ጋራ ተያይዞ ይጠራል። አባ ሻውል በምርጥ ፕላኗ በማትታማው አሥመራ ላይ ያለ ቢኾንም እንደ ጨርቆስ እና መሰል የአዲስ አበባ ሰፈሮች “የድኻ » የሚባል መንደር ነው።  ገዛ መንዳ ሐበሻ ከአባ ሻውል ጋራ የሚጠቀስ ሰፈር ነው። የአራት ኪሎን አሮጌ ቄራ፣ የፒያሳን ሠራተኛ ሠፈር ያስታውሳል።

ማኅደረ አባ ሻውልን ለመልመድ አልተቸገረም። ድህነቱም፣ የአራዳ ልጅነቱም ረድቶታል። ግን አንድ ነገር ሙሉ በሙሉ የአባ ሻውል ልጅ እንዳይኾን ልጓሙን ይይዝበታል። አዲሶቹ ጓደኞቹም እንደ አንዱ የሠፈራቸው ልጅ እንጂ የማንነታቸው አካል አድርገው ለመቁጠር አልፈቀዱም። “ለእነርሱ ኤርትራዊ አይደለሁም፤ ኢትዮጵያዊም አይደለሁም” ይላል። “ለእነርሱ ማኅደረ “አምቼ” ነው።  ብዙዎች የሚጠሩትም “አምቼው” እያሉ ነው።

“አምቼ”…? የምን አምቼ?

“ይኼን ስያሜ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማሁት አባ ሻውል ላይ ነው” አለ ማኅደረ “ስለአምቼነቱ” የሰማበትን ቀን እያስታወሰ።“አንዱ ጓደኛዬ በጨዋታ ላይ እንዲህ አለኝ። “ኻብ ሠፈርካ ዕንታይ ከምዝብልካ ትፈልጥ ዶ?” (ምን እንደምታባል ታውቃለህ?) እኔ አዲስ መጤ ምን ሊሉኝ ይችላሉ በሚል ግርምት “አይፈልጥን” ብዬ መለሰኩለት። ያን ጊዜ “አምቼ” መኾኔን ነገረኝ።” የጓደኛውን ገለጻ ተከትሎ ማኅደረ ከሌሎች ኤርትራውያን “የተለየ ዜጋ” መኾኑ ይሰማው ጀመር። ማኅደረ አይወቀው እንጂ “አምቼ” የሚለው ስያሜ እርሱ አዲስ አበባ እያለ አገልግሎት ላይ ውሎ ነበር።

ጁባ የሚኖረው የ40 ዓመቱ ቢኒያም ፍስሐ ከኤርትራውያን ቤተሰቦቹ ጋራ የኖረው አዲስ አባባ 22 ማዞሪያ አካባቢ ነው። ቢኒያም “አምቼ” የሚለውን መጠሪያ በደርግ ጊዜ አዲስ አበባ እያለ መስማቱን ይናገራል። “ኢትዮጵያ ውስጥ ለተወለደ ኤርትራዊ የተሰጠ መጠሪያ ነበር። ቃሉ የሚገልጸው ኢትዮጵያ ውስጥ መገጣጠሙን ነው” ይላል። መጠሪያው በአንድ ወገን ኤርትራዊ ከኾኑ ወይም ከሁለት ኤርትራውያን ወላጆች ለተወለዱ ዜጎች የሚውል ነው። ስሙ የተወሰደው አዲስ አበባ ከሚገኘው እና በኢትዮጵያ መንግሥት እና በጣሊያኑ የመኪና አምራች ድርጅት ፊያት መካከል በተደረገው ስምምነት ከተቋቋመው “አምቼ”(AMCE) ኩባንያ ነው። የመኪናው አካላቶች ጣሊያን ተመርተው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚገጣጠሙ ሁሉ “አምቼዎች” ኢትዮጵያ ውስጥ “የተገጣጠሙ” የሚል ትርጓሜ ይሰጣል።

አምቼነት ከኤርትራ ጋራ ብቻ አይቆራኝም። ከኢትዮጵያ በተለይም ከአዲስ አበባ ጋራ ባለው ጥልቅ ትሥሥርም ይገለጻል። አሥመራ ላይ “አምቼዎች” በነገረ ሥራቸው ተለይተው ይታወቃሉ። “ብዙ ኤርትራውያን አማርኛ ቋንቋን የሚናገረው አማራ ብቻ ይመስላቸው ነበር። ከ1990 ዓ.ም በኋላ ብዛት ያላቸው አምቼዎች ከኢትዮጵያ ተባርረው አሥመራን አጥለቀለቋት” ይላል ቢኒያም። ከዚያ በኋላ አምቼዎችን አሥመራ ውስጥ ለመለየት ቀላል ነበር። አማርኛ የሚናገሩ፣ በአረማመዳቸው፣ በአለባበሳቸው፣ በአንጻራዊ መልኩ በተላበሱት ግላዊ ነጻነት ይታወቃሉ። የአማርኛ ሙዚቃ በአሥመራ እንግዳ በኾነ መልኩ በስፋት የሚያዳምጡትም አምቼዎች ነበሩ።

“አምቼ” መባል የመገለል ስሜት የሚፈጥርባቸው እንዳሉ ሁሉ ብዙዎች እንደማንነታቸው መገለጫ ይጠቀሙበታል። እንዲያውም የኩራት ምንጭ አርገው የሚወስዱትም አሉ። ኢየሩሳሌም ኀይሌ የከፈተችው “አምቼነቴን እወደዋለሁ” የሚለው አምቼዎች እየተገናኙ የሚጨዋወቱበት የፌስቡክ ገጽ በየቀኑ አባላቱን እያበዛ ነው። በመላው ዓለም የተበተኑ አምቼዎች እየተገናኙ  ስለገጠማቸው ነገር ሁሉ የሚወያዩበት ገጽ ነው።

“አምቼ”ዎች በቁጥር ምን ያህል እንደኾኑ የተጨበጠ ወይም በጥናት የተደገፈ ማስረጃ ባይኖርም በስያሜው የሚጠሩ አንዳንዶች ግን “አምቼ”ን እንደ የኤርትራ 10ኛው ብሔር አድርገው ይቆጠሩታል። የ“አምቼ”ዎች ትክክለኛ አኀዝ ባይታወቅም ከጦርነቱ በኋላ ከኢትዮጵያ የተባረሩ ኤርትራውያኖች ቁጥር 70ሺሕ እንደሚደርስ  መረጃዎች ይጠቁማሉ።

ማነው የተባረረው?

እንደ አምነስቲ ኢንተርናሽናል መግለጫ  ከሆነ በደንበር ጦርነቱ ወቅት  ከኾነ  አብዛኛዎቹ ረዥሙን የሕይወት ዘመናቸውን በኢትዮጵያ ያሳለፉ ናቸው።  በ1990 ዓ.ም ወደ ኤርትራ በመጀመሪያ ዙር በተባረሩ ላይ በተደረገ ሰርቬይ 59 በመቶ የሚኾኑት ከ25 እስከ 60 ዓመት የሚኾነውን ጊዜያቸውን ያሳለፉት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው። ሁሉም በሚባል መልኩ የኢትዮጵያ ዜግነት ያላቸው ሲኾኑ ብዙዎቹም በኤርትራ ሕዝበ ውሳኔ ያልተሳተፉ ነበሩ።

በ1985 ዓ.ም በተደረገው የሕዝበ ውሳኔ ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ ከነበሩ እና ድምፅ ለመስጠት ከተመዘገቡ 57,710 ትውልደ ኤርትራውያን መካከል 99.5 በመቶ የሚኾኑት ነጻነትን የመረጡ ሲኾን 204 ሰዎች ብቻ ከኢትዮጵያ ጋራ መኖርን መርጠዋል። ከአምስት ዓመት በኋላ የኢትዮጵያ መንግሥት ለ“አገር ደኅንነት ስጋት ናቸው” በሚል ብዛት ያላቸውን ትውልደ ኤርትራውያን ከኢትዮጵያ አስወጥቷል። ብዙዎቹ ትውልደ ኤርትራውያንን ከአገር እንዲወጡ የተደረገው ህግሐኤ (ህግደፍ)ን በገንዘብ በመደገፍ እና ትሥሥር በመፍጠር ተወንጅለው ነበር። በቀጣዩ ዓመት 1991 ዓ.ም በሳምንት ቢያንስ እስከ 1500 ዜጎች ከኢትዮጵያ ሲባረሩ ነበር።

አብዛኛዎቹ ተባራሪዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የሥራ መስኮች ተሠማርተው የነበሩ ናቸው። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አጣሪ ልዑክ ቁጥራቸው 250 በሚደርስ የትውልደ ኤርትራውያን ቡድን ላይ ባደረገው ማጣራት መምህራን፣ የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኞች፣ ሜካኒኮች፣ ነጋዴዎች እና የዩኒቨርስቲ መምህራንም ጭምር ከተባራሪዎቹ ውስጥ ተካተው ነበር። ከዚህ ቡድን ውስጥ አንድ የሕክምና ባለሞያ እና ሁለት መነኩሴዎችም ነበሩበት። አብዛኛዎቹ ዕድሜያቸው ከ60 በላይ የነበረ ሲኾን ኤርትራን ረግጠው የማያውቁ  እና ትግርኛ ቋንቋ የማይናገሩ ነበሩ።

ተባራሪዎቹ ወደ ኤርትራ የሚወሰዱት በአራት የድንበር አቅጣጫዎች ነበር። ብዙዎቹ ወደ አሥመራ የገቡት በኦምሃጀር- ተሠነይ- አሥመራ ሲኾን፣ የተወሰኑ በቀይ መስቀል ተባባሪነት በአሰብ በኩል ወደ ኤርትራ ተሸኝተዋል። ጥቂቶች የጦርነቱ ግንባር በነበረችው ዛላምበሳ እና መረብ ዓዲዃላ በኩል ወደ አሥመራ ተጉዘዋል። ሌሎች ደግሞ ወደ ኤርትራ ሳይኾን ወደ ኢትዮጵያ የጠረፍ ከተሞች ሞያሌ እና ጅቡቲ ተወስደው ከአገር እንዲወጡ ተደርገዋል።

ከካምፓላ 73 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ጂንጃ ከተማ የሚኖሩ እና በወቅቱ ወደ ኤርትራ የገቡትን ዜጎች በመቀበል ሂደቱ ላይ  ተሳታፊ የነበሩ አንድ ውስጥ አዋቂ ተባራሪዎቹ ወደ አሥመራ ሲገቡ የነበረውን ስሜት ለአዲስ ነገር እንዲህ ሲሉ ያብራራሉ፦  “የመጀመሪያውን ዙር ተባራሪዎች ስንቀበል የነበረው ከፍተኛ የቁጭት ስሜት ነበር። በከፍተኛ ስሜትም ነበር። የመጀመሪያዎቹ ተፈናቃዮች አሥመራ ዩኒቨርስቲ እንዲያርፉ ተደረገ፤ ዘመድ ያላቸው በየዘመዶቻቸው እንዲሄዱ ተደረገ። በብዙዎቹ ተባራሪዎች ላይ የላቀ ቁጭት እና ግራ መጋባት ይታይ ነበር።” ይላሉ።

“ሙሉ ቤት እና ሀብት የነበራቸው አባዎራዎች ብርድ ልብስ እና አንሶላ ለመቀበል ሲሰለፉ ለብዙዎቹ አንገት የሚያስደፋ ነበር። እስካሁን ድረስ ያልሻረ ጠባሳ ነው” ሲሉ የተፈጠረውን ችግር ያስረዳሉ። የችግሩ መጠን የተባባሰው ደግሞ የተባራሪዎች ቁጥር በየቀኑ እየናረ ሲመጣ እና የአሥመራ አቅም ከሚችለው በላይ ሲኾን ነበር። ያውም ብዙዎች ከመላው የቤተሰባቸው አባላት ጋራ የመምጣት ዕድል ባለገኙበት ኹኔታ።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሕፃናት ፈንድ (ዩኒሴፍ) በሁለት የተባራሪዎች መቀበያ ጣቢያ ባደረገው ሰርቬይ በሰኔ 1990 ወደ ኤርትራ ከተባረሩት ውስጥ 63 በመቶ የሚኾኑት አዋቂ መላሾች ከልጆቻቸው ተለያይተው እንደመጡ ተናግረዋል። ብዙዎቹም ሀብት እና ንብረታቸውን በወጉ ለማደራጀት እንኳ ዕድል አልነበራቸውም። ይህን መሰሉ ትውልደ  ኤርትራውያንን ሰብአዊነት በጎደለው መልኩ ከኢትዮጵያ የማስወጣቱ ሂደት በወቅቱ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ዓለም አቀፍ ነቀፋ ያሰነዘረ ነበር። ነቀፋው እና ትችቱ በወቅቱ በነበረው ኹኔታ ላይ ብቻ የተወሰነ እና ተባራሪዎች ከዓመታት በኋላ ሊገጥማቸው የሚችለውን የማኅበራዊ ኑሮ ቀውስ ከግምት ውስጥ የከተተ አልነበረም።

ይህ ሁሉ ታሪክ ከተፈጸመ ከዐሥር ዓመት በኋላ ያለው የተባራሪዎች በተለይም የ“አምቼ”ዎች ሕይወት በምስቅልቅል ኹኔታዎች፣ በማንነት ቀውስ እና በግራ መጋባት የተሞላ ነው። ለአዲስ ነገር ታሪካቸውን ያጋሩ “አምቼ”ዎችም ይህንኑ እውነታ ይቀበሉታል። ለደኅንነት በመስጋት ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁት ኹኔታውን በቅርበት ሲከታተሉ የነበሩ የጂንጃው ውስጥ አዋቂም ወደ ኤርትራ የገቡት አምቼዎች የተለያዩ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሥነ ልቡናዊ  ችግሮችን መጋፈጣቸውን ይመሰክራሉ።

የአምቼነት  ዕዳ

እንደ ማኅደረ ያሉ ብዛት ያላቸው የትውልደ ኤርትራውያን ልጆች እና ወጣቶች አሥመራን ካጥለቀለቁ በኋላ ያጋጠማቸው ያልጠበቁት እና ካደጉበት በብዙ የሚራራቅ ነበር። ብዙዎቹ  አሥመራን እና ነዋሪዎቿን ሲያስተውሉ እጅግ ወግ አጥባቂ እና የውጭ ሰው እና አስተሳሰብ በቀላሉ የማያስገባ ዝግ መኾናቸው ተረዱ። እነርሱ ካላቸው አንጻራዊ የኾነ “ተራማጅ” ማኅበራዊ መስተጋብር አንጻር ከአሥመራ ነባር ነዋሪዎች ጋራ መዋሃድ እጅግ ፈታኝ ነበር። የሚናገሩት ቋንቋ አማርኛ በመኾኑ አምቼዎች ሙሉ በሙሉ ከአሥመራ ነዋሪዎች ጋራ እንዳይዋሃዱ አርጓቸዋል።

“በአረማመድ ሳይቀር ማን አምቼ እንደኾነ ትለያለህ” ይላል ቢኒያም። “አምቼ”ዎች በሚሰሙት ሙዚቃም ተነጠለው ይታወቃሉ። የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ጫፍ በደረሰበት ሰሞን እንኳን በአሥመራ እንዲሁም ከረንን በመሰሉ አነስተኛ ከተሞች ውስጥ በሚገኙ ትናንሽ የመዝናኛ ቤቶች ውስጥ ሳይቀር የአማርኛ ሙዚቃ እንደልብ ማጫወታቸው በጤና አልታየም። ይህንን ተከትሎም የአማርኛ ሙዚቃዎችን በየምሽት ክበቦች ማጫወት እንዲቀር ታግዷል።

“ከመባረሩ ሂደት ጋራ በተያያዘ ብዙዎቹ የሥነ ልቡና ተጽዕኖ ውስጥ ነበሩ።” ይላል ቢኒያም። ማንነታቸው ሁለት ቦታ የተሰፋ ነው። አዲስ አበባ እና አሥመራ። ማኅደረም ከዚህ አልወጣም።  ከአደገበት ቀዬ ተነቅሎ ያለ ውዴታ እና ፈቃዱ፤ በሚያዋርድ እና የሰውነት ክብርን በሚነካ መልኩ ወደ ኤርትራ መላኩን ያብሰለስለዋል። ዛሬ ልቡ ለኤርትራዊነት ያጋድላል። ግን ኤርትራዊ በመባልም ምሉዕነት አይሰማውም።  “የጓደኞቼ ፍቅር እና ወዳጅነታቸው ለአፍታ ባይጓደልብኝም ስያሜዋ አንዳች ክፍተት በልቤ ውስጥ ፈጠረች። ኤርትራንም እንደ ኢትዮጵያ ጊዜያዊ መጠለያዬ እንጂ ቋሚ አገሬ ለማለት የማልደፍራት እንደኾነች ገባኝ። ኢትዮጵያዊ ነኝ እንዳልል መባረሬ መልሱን ሰጥቶኛል” ሲል የተፈጠረበትን ግራ መጋባት ያስረዳል። “የማልክደው ነገር ከኢትዮጵያ በመባረሬ ለኤርትራ ያለኝን ፍቅር መጨመሩ ነው።”

ማኅደረ ያንን ጊዜ የሕይወቱ “አስጨናቂ” እና “አስቸጋሪ” ወቅት አድርጎ ይቆጥረዋል። ከሁሉ ፈተና የኾነበት ገቢ ማግኘት አለመቻሉ ነበር። የአባቱ ዘመዶች የመረዳዳት ጠንካራ ባህል ታክሎበት እንኳ ኑሮን መግፋት እንደ አለት ጠጥሮበት ነበር፡፡ ተንቀሳቅሶ ለመሥራትም የሚያስችል ምንም ዐይነት ቀዳዳ አልነበረም።

ለአብዛኛዎቹ “አምቼ”ዎችም ሕይወት እንዲያ ነበረች። ከብሔራዊ አገልግሎት ከተረፉ አሥመራ ውስጥ አለ የተባለውን ማንኛውንም ሥራ በመሥራት ይታወቃሉ። በብዙ የአሥመራ ነዋሪዎች የማይደፈሩ እንደማስተናገድ ያሉ ሥራዎችን ሳይቀር ይሠራሉ። አንዳንድ እንስቶችም ተገደው ወደ ሴተኛ አዳሪነት ገብተዋል። አንዳንዶችም በአሥመራ ባልተለመደ ኹኔታ ለአደገው ዝርፊያ ተጠያቂ የተደረጉት እነርሱው ናቸው።  “ሌብነት፣ ማታለል እና በቡድን መደባደብ ከአምቼዎች ጋራ ብቻ እየተያያዘ የሚነሳ ነገር ኾኖ ነበር” ይላል መኖሪያውን ናይሮቢ ያደረገው በፀጋ ሳህለ። ይህ ተደራራቢ ከመጥፎ ነገሮች ጋራ የመዛመድ ችግር የገጠማቸው አምቼዎች የመገለል እና የራሳቸውን ክበብ በመሥራት መራቅን እንዲመርጡ አድርጓቸዋል።

የኤርትራ መንግሥት የሚከተለው ዜጎችን በወታደራዊ አመለካከት የመቅረጽ ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ ለአምቼዎች የሚመች አልኾነም። የኤርትራ መንግሥት መሪዎች አክራሪ የኤርትራዊ ብሔርተኝነት አቀንቃኞች ናቸው። ይህ የአምቼ ማንነት ከተገነባበት መሠረት ጋራ የሚፋለስ ነው። የአምቼዎች ብሔራዊ ማንነት በኢትዮጵያም በኤርትራም ፖለቲከኞች እና ልሂቃን ዘንድ  እውቅናም ገና አልተሰጠውም።

አምቼዎች ማንነታቸው የተገነባው በሁለት ጠንካራ ብሔርተኛነትን በሚያቀነቅኑ (ኢትዮጵያ እና ኤርትራ) ወገኖች መካከል ነው። ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነትም ኾነ የኤርትራ ብሔርተኝነት አንዱ ለአንዱ እውቅና የሚሰጡ አይደሉም። ተፎካካሪ ናቸው።  የሁለቱም ብሔርተኝነት አቀንቀኞች “ቀናተኞች” ናቸው። አንደኛው ሌላውን አይቀበልም። አሥመራ የሚናኘው የብሔረተኝነት አመለካከት “ለ30 ዓመት ከኢትዮጵያ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት በተደረገውን ጦርነት እና ድል “ ውስጥ የበቀለ እና ያደገ ነው። የኢትዮጵያ ብሔርተኝነትም ለኤርትራ ብሔርተኝነት እውቅና የሚሰጥ ሳይኾን እንደ ስኅትተ እና ክህደት ይቆጥረዋል። የአምቼዎች ማንነት የተገነባው ደግሞ የአንዱን የብሔርተኝንት እንቅስቃሴ በመናድ እና የሌላኛውን በመደገፍ ሳይኾን በሁለቱ የብሔርተኝነት አጽናፎች መካከል ያለውን መካከለኛ ቦታ ይመርጣል። አምቼዎች ማንነታቸውን የሚገልጹት በሁለቱ ብሔራዊ “ቤቶቻቸው” ነው። ሁለቱንም እንደቤታቸው ያያሉ።  ነገር ግን ከሌላኛዋ “ቤታቸው” ኢትዮጵያ በግድ የተነቀሉ ናቸው። አምቼዎች በትዝታ እና በቁጭት ወደ አዲስ አበባ በሐሳብ መመለሳቸው አልቀረም። ላደጉባት አዲስ አበባ ልዩ ፍቅር እና ግምት አላቸው። ከአዲስ አበባ የተነጠሉበት መንገድ ደግሞ አዲስ አበባን በበጎ ብቻ እንዳያስታውሷት አርጓቸዋል።

አምቼዎች ኑሮ በአሥመራ እጅግ ፈታኝ ኾኖባቸዋል። ኢኮኖሚው እና ማኅበራዊው ችግርም ቶሎ ሊቀረፍ ያልቻለ ነበር። ብዙዎቹ ከድንበር ጦርነቱ በኋላም አሁንም ብሔራዊ አገልግሎት ከመስጠት አልወጡም። መቼ እንደሚወጡም አቶ ኢሳያስ አፈወርቂ እና እግዜር ብቻ የሚያውቁ ይመስላል። አሥመራ ላይ ያለው የአቶ ኢሳያስ አስተዳደር በየጊዜው ፍፁም አምባገነንነቱን እያጠናከረ መሄዱ የአምቼዎችን ሕይወት መፈናፈኛ እንዳይኖረው አድርጎታል። እንደ ማኅደረ ያሉት ግን ተሳክቶላቸው አገራቸውን ጥለው ዳግም ስደት ገብተዋል።

ዳግም ስደት……ዘጸአት ለአምቼ

አሥመራም ያልደላቻቸው ብዙ “አምቼዎች” ኤርትራን ለመልቀቅ ድንበር ማቋረጥ ጀመሩ። ወደ የመን፣ ኢትዮጵያ እና ሱዳን። ለደላሎች ብዙ መክፈል ግድ ይላል። ገንዘብ ያላቸው ብቻ ለቀናት የእግር ጉዞ በማድረግ ከኤርትራ ደንበር ጠባቂዎች ተደብቀው ወደ ከሰላ (ሱዳን) በሕገ-ወጥ መንገድ ለመውጣት ይሞክራሉ። የተሠነይ-ከሰላ መንገዱ አንዱ ሲኾን ከኤርትራ ለመውጣት እስከ 4ሺሕ ዶላር የሚቀበሉት አስተላላፊዎች ሌሎችም በሮች አሏቸው። የቻሉ ይወጣሉ፤ ሌሎች ደግሞ ተይዘው ይታሠራሉ ወይም ይገደላሉ።

በዚህ መልክ ኤርትራን ለቀው ከተሰደዱት መካከል አንዱ ቢኒያም ነበር። እርሱ እንደ አብዛኛዎቹ አምቼዎች በድንበር ግጭት በተነሳው ጦርነት ምክንያት ራሱን አሥመራ ላይ አላገኘውም። በ1983 ዓ.ም ደርግ ሲወድቅ ወደ ኤርትራ ሄደ። ከአዲስ አበባ አስመራ በአውቶብስ እየተመላለሰ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችን፣ ሲጋራ እና ማስቲካ ይነግድ የነበረው ቢኒያም የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ሲነሳ አሥመራ ላይ ነበር፤ ድንበርም ተዘጋ። ብዙዎችም ተባረሩ። ያኔ አሥመራ ላይ መቅረት ግድ ኾነ።

ባለትዳር እና የሁለት ልጆች አባት የነበረው ቢኒያም ንግዱን ቢቀጥልም ከእንድ አስቸጋሪ ነገር ጋር ተፋጠጠ። እንደ ደንቡ የብሔራዊ አገልግሎት ግዴታውን መወጣት ነበረበት። በኤርትራ መንግሥት ሕግ መሠረት ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 40 ዓመት የኾናቸው ዜጎች የብሔራዊ አገልግሎት የመስጠት ግዴታ አለባቸው። ሦስተኛ ልጁን እርጉዝ የነበረችውን ባለቤቱን ጥሎ ላለመሄድ ያልፈለገው ቢኒያም ከባለሥልጣናቱ ጋራ ድብብቆሽ ጀመረ። ቁጥጥሩ ጥብቅ እየኾነ ሲመጣ የቀረው ሁለት አማራጭ ነበር።  ወደ ብሔራዊ አገልግሎት መሄድ ወይም ከሀገር መውጣት።

አገር ጥሎ መውጣት ግን ቀላል አልነበረም። በየቦታው ያሉትን ኬላዎች ማለፍ፣ በአልሞ ተኳሽ ወታደሮች የሚጠበቅ ድንበርን ማለፍ ይጠይቅ ራሱን የቻለ ፈተና ነበር። ከአሥመራ ተሰነይ በአውቶብስ የተጓዘው ቢኒያም ድንበር አቋርጦ ከሰላ ለመግባት የ17 ሰዓት የእግር ጉዞ መሄድ ግድ ኾኖበታል። “እኛ የወጣንበት መንገድ አሪፍ ነበር” ይላል ቢኒያም። የወታደሮች አፈሙዝ የሌለበት፤ ይህን መንገድ የሚያውቁ ሰዎች ግን በወቅቱ “ጫን ያለ” ክፍያ ነበር የሚጠይቁት።

የተጠየቀውን 1500 ዶላር ከፍሎ የሱዳን የድንበር ከተማ የኾነችው ከሰላ የደረሰው ቢኒያም በድንበር ጠባቂ ፖሊሶች እጅ ላይ ይወድቃል። “ከሰላ ስገባ ጀለቢያ አድርጌ ነበር። ጸጉረ ልውጥ ስለኾንኹ በፖሊሶች ተያዝኩ። በኪሴ 3000 ዩሮ እና 200 ዶላር ነበረ። ፖሊሶቹ ራቁቴን አድርገው ፈተሹኝ” ይላል። የኮሎኔል ማዕረግ ካለው ፖሊስ ፊትም እንዲቀርብ ተደረገ። “የሚያውቁት ገንዘብ ዶላር ስለነበር የያዝኩትን 200 ዶላር ሰጠኋቸው። ዩሮውን ስላላወቁት ለቀቁኝ” ሲል እንዴት ለመቋቋሚያ ብሎ የያዘው ገንዘብ እንደተረፈለት ይናገራል። ዛሬ ራሱን ጁባ ከማግኘቱ በፊት ከአገር አገር ዞሯል። ካርቱም- አዲስ አበባ- ናይሮቢ-ሉዋንዳ -ካምፓላ።

አሁን ኬንያ የሚገኘው ማኅደረ ድንበር ከመሻገሩ በፊት ኤርትራውያንን እና አምቼዎችን ማስኮብለል ሥራው ነበር። ከባድ የኾነበትን የአሥመራ ኑሮውን ትንሽ መልክ ያስያዘው ይኼው ሥራው ነበር። ወደዚህ ሥራው ደግሞ ያመጣው የ“ኮምቢሽታቶው ጮሌ” ሚካኤል ነበር። ሚካኤል የአባ ሻወል ሠፈር ልጅ ነው። ነገር ግን ውሎው እና ተግባሩ ኮምቢሽታቶ በመኾኑ ነበር የ“ኮምቢሽታቶው ጮሌ” የሚል ስያሜውን ያገኘው። በጣም ተግባቢ  ነው።

ሚካኤል እና ማኅደረ የተግባቡት የ“ኮምቢሽታቶው ጮሌ” ማኅደረ ዘወትር ከማይጠፋባት “በረኸት ሻይ ቤት” በትዝታ ሲናውዝ ያገኘው ቀን ነበር። “አንቺ አምቼ አሁንም ሠፈር አልለመድሽም ?” አለው ማኅደረን! በቀላሉ ተግባቡ። ወዳጅነታቸው ጠነከረ። ሳምንቱን ሙሉ አይነጣጠሉም። ውሏቸው “ካምቦሎ”፣ “ትራቮሎ”፣ “ፊያት”፣ “ሳንፍራቼስኮ”፣ “አክሪያ” እና ሌሎች ሠፈሮች ኾነ። ማኅደረ አዲስ አባባ እያለ ወደ ሲኒማ ኢትዮጵያም ኾነ ሲኒማ አምባሳደር ብቅ የማለት ልምድ አልነበረውም። በአሥመራ ግን ደንበኛ ኾነ። በ“ሲኒማ አዝመሪኖ” እና በ“ሲኒማ ካፒታል” በየቀኑ ይታደማል። ሚካኤል ይከፍላል፤  ማኅደረ ይዝናናል።

አንድ ቀን የአሥመራ መለያ  የኾነው ካቴድራል ወደ ሚገኝበት  ኮምቢሽታቶ ተያይዘው ነጎዱ። አምባሳደር ሆቴል እዚሁ አቅራቢያ ይገኛል። በአቅራቢያው ወደሚገኝ  ባለ አንድ ፎቅ ወዳለው ቤት ተያይዘው ሄዱ።  “ፈጠን ብለህ ግባ” አለው ሚካኤል ኋላ እና ፊቱን እየተገላመጠ። “የሕንጻውን ዋና በር እንዳለፍኩ ግድግዳ ተደገፌ ጠበቅኹት። ‘ተከተለኝ’ የሚል ትዕዛዝ ብቻ ሰጥቶኝ ነጠር ነጠር እያለ ከፊት ለፊቴ ይመራኝ ጀመር” ይላል ማኅደረ ።

የገቡት ከሕንጻው ጀርባ ካለች አነስተኛ ክፍል ነበር። ሦስት ወጣቶች አትነጋገሩ የተባሉ ይመስል በፀጥታ ተቀምጠዋል። ሚካኤል ንግግር አላበዛም። “በማለዳ ተነስታችሁ እዚሁ እንገናኛለን፤ ቻው” የሚል ቃል እንደተናገረ አንደኛው ወጣት ለሚካኤል በእጁ አንድ ነገር አስጨበጠው። “ተረጋግታችሁ ውጡ” የሚል ትዕዛዝ ብቻ ሰጥቶ በጥንቃቄ ሕንጻውን ለቀቀው ወጡ። የኮምቢሽታቶውን ጮሌ ዋነኛ የገቢ ምንጩ በድብቅ ከኤርትራ የሚወጡ ዜጎች “መርዳት” መኾኑን ማኅደረ ያወቀው በዚያ አጋጣሚ ነበር።

የኮምቢሽታቶው ጮሌ ዋና ሥራ ተጓዦቹ ከአሥመራ እንዲወጡ መርዳት ነው፤ ከዚያ በሻገር ስላለው ደግሞ ሌሎች ባልደረቦቹ ይጨነቁበታል። ከተሳካ እስከ ኢትዮጵያ ወይም ሱዳን ድንበር ያደርሳሉ። ከዚያ በኋላ ያለው ጣጣ የስደተኛው ይኾናል። በወቅቱ በርካቶች በውትድርናው ሥራ የመረራቸው፣ ሳዋን የሚሸሹ እና የተሻለ ኑሮ የሚፈልጉ ወጣቶች ነበሩ። ውቧ ግን ሕይወት አልባዋ አሥመራም ሰልችታቸው ነበር። ለእርሱ ብቻ ሳይሆን ለብዙ አምቼዎች። የመንግሥት ቁጥጥር ከፍተኛ በመኾኑ ዜጎችን ማስኮብለል ቀላል ሥራ አልነበረም። እጅግ ጥንቃቄን የሚሻ ነው። ከሞት ጋራ አንገት ለአንገት ተናንቆ የሚሠራ ነው።

ከቀናት ምክክር እና ልምምድ በኋላ ማኅደረ የሚካኤል ረዳት ኾነ። የተሰጠው ሚና ደግሞ ከኢትዮጵያ የተባረሩ እና መመለስን የሚሹ አምቼዎችን ማገናኘት ነበር። ሥራው  መልካም ነበር፤ ገቢ አለው። ነገር ግን ሕይወት ከወዲህ ወዲያ የሚያላጋቸውን ለጋ ወጣቶች አደጋ ባለው ጉዞ ለማሾለክ ለህሊናው  ፈታኝ ኾኖበታል። ግን ሕይወት ሌላ የተሻለ ምርጫ አልሰጠችውም። “አስገራሚው ነገር በየቀኑ ከሁለት ያለነሰ ሰው ለመኮብለል እንደሚፈልግ ማወቄ ነበር። አገር የሚሰደድ ነው የሚመስለው። እንደዚህ ጥብቅ የመንግሥት ቁጥጥርም እያለ የሚኮበልል ሰው ማግኘት ሳይኾን እንዴት ለማስኮብለል እንደሚቻል ነው የሚቸግረው” ይላል።

ማኅደረ በመጨረሻ ራሱን ለዳግም ስደት አጨው። አሥመራ ቢቆይ ከአባ ሻውል እስከ ኮምቢሽታቶ…እንደ ልብ ወዲህ ወዲያ ሲል እንደማይኖር ያውቀዋል። ሳዋ አፉን ከፍቶ ይጠብቀዋል። “በአዝመሪኖ ያለው ቆይታዬም በሳዋ ግዞት መጠናቀቁ ስለማየቀር ከወዲሁ ልኮብልል ስል ራሴን መከርኩት” ይላል ውሳኔ ላይ ስለደረሰበት ወቅት እና ኹኔታ ሲያብራራ። ለስደት የመረጠው መንገድ ግን ሌላ ፈተና ይዞ መጣ። ኢትዮጵያን እንደ መሸጋገሪያ ድልድይነት ቢወስዳትም የኤርትራን ድንበር አልፎ ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ የማንነት ጥያቄው አፍጥጦ መጣበት “እኔ የማን ነኝ?” የሚል።

“አሥመራን እስከምለቅ በስጋት ውስጥ ጥያቄውን አዳፈኜው የነበረ ቢኾንም አክሱም ከተማ ስደርስ ዐይኑን አፍጥጦ መጣብኝ” ይላል።  ከማኅደረ ጋራ አብረው የኮበለሉት ወደ ሽመልባ መጠለያ ካምፕ ሲገቡ እርሱ ግን ወደ አዲስ አበባ ተጓዘ። አዲስ አበባ ጥቂት ከሰነበተ በኋላ ወደ ኬኒያ አቀና። ብዛት ያላቸው አምቼዎችም የማኅደረን መንገድ ተከትለዋል።

ሥርጭት በምሥራቅ አፍሪካ

አምቼዎች ከአዲስ አበባ እና አሥመራ ውጭ በመላው የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ተበትነዋል። በተለይ በምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ካርቱም፣ ጁባ፣ ካምፓላ፣ ናይሮቢ፣ ሞምባሳ፣….እና በመላው ዓለም ይገኛሉ። ምሥራቅ አፍሪካ ላይ ደግሞ በብዛት ይገኛሉ። በተለይ  ጁባ እና ናይሮቢ።

ከሞይ ጎዳና ዳር ቆሞ ለሚመለከት ናይሮቢ በግልጽ በሚታይ ኹኔታ በሁለት የተከፈለች ከተማ ነች። ዌስትላንድ (Westland) እና ኢስትላንድ (Eastland) በሚል። ምዕራቡ የከተማዋ ክፍል በአረንጓዴ የተሸፈነ፣ አልፎ አልፎም ጥቅጥቅ ያሉ ደኖች ያሉበት፣ በብዛት ከፍተኛ ገቢ ያላቸው የኬንያ ዜጎች፣ ሕንዶች እና የሌሎች አገራት ዜጎች የመኖሪያ ሥፍራ እና መዝናኛዎች የበዙበት ነው። ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ስደተኞች ከሚኖሩባቸው የኬኒያ መንደሮች መካከል አንዱ የኾነው “ሐርሊንግሃም” በዚሁ ምዕራባዊ የናይሮቢ ክፍል (ዌስትላንድ) ይገኛል።

ወደ “ያያ የንግድ ማዕከል” የሚወስደውን መንገድ ተከትሎ ለሚጓዝ ሁሉ ከዳገቱ ላይ ኾኖ “ሐርሊንግሃም” የሚባለው አካባቢ ይቀበለዋል። የአካባቢው ሰላማዊ መኾን እና ማራኪነት አቅሙ ያላቸውን ሐበሾች የሚስበውን ያህል፣ በሌላ ጎኑ ደግሞ በአነስተኛ ዋጋ በጋራ ለመኖር ለቆረጡ የሐበሻ ስደተኞችም መሰባሰቢያ ስፍራ ነው። ሐርሊንግሃም ለመድኀኒዓለም ቤተክርስቲያን ቅርብ ኾኖ መገኘቱም የበለጠ ተመራጭ አድርጎታል። ዐይንዎን በአካባቢው በማይጠፉት ሐበሾች ላይ ያሳርፉ። ምን አልባት ለናይሮቢ አዲስ ከኾኑ ኤርትራዊ፣ ኢትዮጵያዊ  ከሚለው መለያ በተጨማሪም “አምቼዎችንም” እዚህ ያገኟቸዋል። አብዛኞቹ አምቼዎች በሁለቱ ወገኖች መካከል የመዋለል ስሜት ይሰማቸው እንጂ ወደ ኤርትራዊነት ማጋደላቸው አልቀረም፡፡ በተለይም ግማሽ ኤርትራውያኑ በቂ የሚሉትን ምክንያት ያሰቀምጣሉ፡፡ ለአብዛኞቹ ከኢትዮጰያ ወገን ካሉ ዘመዶቻቸው ይልቅ ከኤርትራ በኩል የሚዛመዱ የመረዳዳት ባህላቸው ጠንካራ መኾን ለዝንባሌያቸው ምክንያት ነው፡፡ በፀጋም ይሄን ሃሳብ ያጠናክራል፡፡ “በስመ ኤርትራዊ እርዳታ ብትጠይቀ የሚነፍግህ የለም፡፡ አገር ቤት ብትሄድ ደግሞ ሰርጉም ሃዘኑም ለብቻህ ስለማትወጣው መደጋገፉ የጠነከረ ነው”

በናይሮቢ ያለው የስደተኞች የአኗኗር ዘይቤም ይሄን የሚያሳይ ነው፡፡ ኤርትራውያኑ (አምቼዎቹን ጨምሮ) በአንድ ስፍራ አጀብ ብለው መኖርን ይመርጣሉ፡፡ ለአንዱ በተላከው የድጎማ ገንዘብ የተቸገረ ወገናቸውን ጭምር ይረዱበታል፡፡ መጠለያ የሌላቸውን በዙር በየቤታቸው ከማስጠለል አንስቶ ወርሃዊ የቤት ኪራይ በመክፈል ጭምር አለኝታነታቸውን ያሳያሉ፡፡

የሐርሊንግሃም ጉዳያችንን ከጨረስን “አምቼዎች” በስፋት ወደሚኖሩበት ወደ ምሥራቃዊው ናይሮቢ እናዝግም፤ ከአምቼው ማኅደረ ጊላይ ጋራ። የናይሮቢ ምሥራቁ ክፍል ከምዕራቡ በተቃራኒው ብዙ ለምለም ነገር የማይታይበት፣ ድህነት የደቆሳቸው መንደሮች በብዛት የሚገኙበት እንዲሁም ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚካሄድባቸውን ሥፍራዎች አካቶ የያዘ ነው። ከ“ኢስሊ” ሌላ “ቻይሮድ” ወደ ሚባለው ሰፈር ቢያቀኑ ብዛት ያለቸውን ሐበሾች ችምችም ባለው መንደር መካከል ያገኟቸዋል። በዚህ ሥፍራ ዳር እና ዳር በአማርኛ የተጻፉ ማስታወቂያዎችን ይመለከታሉ።

ከ“ካተሪና ሎጅ” ፊት ለፊት “አሥመራ ሆቴል” ጎላ ብሎ ይታያል። ኢትዮጵያውንም በብዛት ቢገኙም የኤርትራውያኑን ያህል አይኾኑም። ብዙኀኑ በምግብ ሥራ፣ በችርቻሮ እና በመጠጥ ንግድ ራሳቸውን ያስተዳድራሉ። አካባቢው ከኪስዋሂሊ እና ከእንግሊዝኛ ቋንቋ ይልቅ ትግርኛ እና አማርኛ ጎልተው የሚነገሩበት ነው።

ካሪያኮር እና ፓንጋኒ የሚሉት አካባቢዎች በሐበሻ የሚዘወተሩ ቢኾንም የኤስሊን ያህል ግን ሐበሻን አያስተናግዱም። ኤስሊ የሶማልያውያን የበላይነት እየነገሠ የመጣበት ትልቁ የንግድ ሥፍራ ነው። በብዙ መልኩ ከአዲስ አበባው መርካቶ ጋራ ይቀራረባል። ይኹንና ኤስሊ የሚንቀሳቀሰውን የዶላር መጠን መርካቶ በዓመት ለማንቀሳቀስ አቅም ያለው አይመስልም። በዚህ ወከባ እና ግርግር በበዛበት ሥፍራ ሐበሾችም የራሳቸው ድርሻ አቸው። ሁለተኛ፣ ዘጠነኛ፣ ዐሥረኛ እና ዐሥራ አንደኛ የሚባሉት መንገዶች በብዛት ሐበሾችን የያዙ ክፍሎች ናቸው። ሚሚ ሱቅ፣ ቴዲ ሙዚቃ ቤት፣ የባህል መደብር . . የመሳሰሉት የአማርኛ ማስታወቂያዎች ጎልተው የሚታዩት ግን በተለይ በዘጠነኛ እና በዐሥረኛ መንገዶች ነው።

በናይሮቢ ጉራንጉሮች ውስጥ የእሱን መሰል ታሪክ ያላቸው አሚቼዎች ጉዞ ገታ ያድርጉ እና ወደ ደቡብ ሱዳን ዋና ከተማ ጁባ ይጓዙ። ከናይል ወንዝ አቅራቢያ ከተሠራው እና የጁባ ዐይን ከኾነው “ብሪጅ” ሆቴል ተነስተው ጉዞዎን ቢያደርጉ እዚህም እዚያም ሐበሾችን ይመለከታሉ። “ኮኞ ኮኞ”፣ “ገበል ኩጁ”፣ “ኒው እና ኦልድ ከስተመስ”..እንዲሁም በመላዋ ጁባ ቢዘዋወሩ እንደልብ የሚያገኙት እነርሱኑ ነው። ጁባ ሮድ በሚገኘው “ኩሽ ሆቴል” ገብተው ዐይንዎን ጣል ቢያደርጉ እዚህም እዚያም አበሾች ክብ ሠርተው ሲያወጉ ስልክ ሲደውሉ፣ ጥሪ ሲቀበሉ ያያሉ።

ጁባ የደቡብ ሱዳን ልብ የኾነች የንግድ ከተማ ነች። ወደ ምግብ ቤቶች ጎራ ሲሉ የሚያስተናግዱዎትም አዲስ አባባ የሚያውቋቸው ኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ሊኾኑ ይችላሉ።  ጁባ ነፍስ የምትዘራው በኤርትራውያን እና በኢትዮጵያውያን ነው። ከከፍተኛ የመንግሥት አማካሪዎች እስከ ሾፌር፣ ነጋዴ፣ አስተናጋጅ፣ ወያልነት….ድረስ ጁባ ትዘወራለች። አምቼዎች ከኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን መሳ ለመሳ ኾነው ሕይወታቸውን ይገፋሉ። ቢኒያም እዚህ ይኖራል። ማኅደረ ደግሞ ኬንያ። ብዙዎች “አምቼዎች” እንደ ቢኒያም አሊያም እንደ ማኅደረ ዕድለኞች አልነበሩም። ዛሬ በሕይወት ተርፈው ታሪካቸውን ለማውራት ዕድሉን አላገኙም።

አሳዛኙ ዕጣ

አንዳንዶቹ እጅግ ዘግናኝ በሚባለው የባድመ ጦርነት ከለብ ለብ ሥልጠና በኋላ እንዲሳተፉ ተደርገዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ያባረራቸው ብዛት ያላቸው አምቼዎች አሥመራ በገቡ በስድስት ወር ጊዜ ወስጥ ወደ ሳዋ ወታደራዊ ማሠልጠኛ እንዲሄዱ ይደረጉ ነበር። የሳዋ ስምንተኛ እና ዘጠነኛ ዙር ሠልጣኞች ብዙዎቹ አምቼዎች ናቸው። ሥልጠናውን እንደጨረሱ እጅግ ዘግናኝ እና ለሰው ሕይወት ደንታ ባልነበረው የባደመ ጦርነት ተማገዱ። ብዙዎቹም ሕይወታቸውን እና አካላቸውን አጥተዋል። አሳዛኙ ዕውነታ ደግሞ “አምቼ”ዎች በጦርነቱ ወቅት በሁለቱም ወገኖች የማይታመኑ መኾናቸው ሕይወታቸውን የበለጠ ያከፋው እንደነበር አዲስ ነገር ዩጋንዳ -ጂንጃ ውስጥ ያነጋገራቸው ለጉዳዩን ቅርበት የነበራቸው ግለሰብ ያስረዳሉ።

“ጦርነቱ ላይ ስለ ተሳተፉት ወጣት ትውልደ ኤርትራዊ ዜጎችን (አምቼዎችን) አስብ።  በተለይ አንዳንዶቹ ወጣቶቹ ኢትዮጵያዊ ነን ብለው የሚያስቡ፤ ከአዲስ አባባ ውጭ ሌላ ከተማ ዐይተው የማያውቁ ነበሩ” ይላሉ ውስጥ አዋቂው። “በሕይወትህ አስበህ እና ገምተህ በማታውቀው መልኩ ለማታውቀው አገር ወታደር ኾነህ ራስህን ብታገኘው ምን ይሰማኻል? ከእኛ ወዲያ የአበደ አለ?” ሲሉ በወቅቱ የነበረውን ኹኔታ በጥያቄ መልክ ያስቀምጡታል።

ማኅደረ ይህን መሰል ታሪኮችን ኖሯቸዋል። ተረት የሚመስሉት እውነተኛ የትራጄዲ ታሪኮች ቁጥር ስፍር የላቸውም። “ከአዲስ አባባ ወጥቶ የማያውቅ የ18 ዓመት ልጅ ከአባቱ ጋራ ወደ ኤርትራ ተባረረ፤ ለምን እንደተባረረም በቅጡ ያልተረዳ ወጣት። አሥመራ በገባ በስድስት ወሩ ሳዋ ገባ፤ ባድመ ላይ ሞተ። ለምን ሞተ?…” ማኅደረ ይጠይቃል። አባቱ የልጃቸውን ሞት ከሦስት ዓመት በኋላ ሰሙ። ባዶ ሕይወት። የማኅደረ- አምቼ ትዝታዎች፤ በናይሮቢ።

ከ10ኛ ብሔረሰብ ወደ አምቼዎች ዓለም

“አምቼ”ዎችን አንዳንዶች “ግራ የተጋቡ” ሲሉ ይገልጿቸዋል። የአዲስ ነገር ዘጋቢዎች ይህን ዘገባ ለማጠናቀር በተንቀሳቀሱባቸው የምሥራቅ አፍሪካ የተለያዩ ከተሞች ናይሮቢ፤ ካምፓላ፣ ጁባ፤ ካርቱም፣..እና ሌሎች ትንንሽ ከተሞች ግን “አምቼ”ዎች ያላቸው ማኅበራዊ ፋይዳ አይተዋል። አምቼዎች “ድልድዮች”፣ “ሰላም አስከባሪዎች” የሚሉ ስያሜዎች ያገኙትም በማኅበራዊ መስተጋብር ላይ ባላቸው አበርክቶት ነው።

“አምቼ”ዎች የኢትዮጵያን እና የኤርትራን ሕዝቦች የሚያገናኙ፤ በሁለቱም ውስጥ የሚገኘውን ደካማ እና ጠንካራ ጎን የሚረዱ ናቸው። በሁለቱ ሕዝቦች መካከል አንዱ ለአንዱ ያለውን አሉታዊ ግምት ለመፋቅ በአንድ ተመሳሳይ ወቅት ለኤርትራም፤ ለኢትዮጵያም ወግነው የሚከራከሩ ናቸው።

በጁባ፣ ናይሮቢ፣ ካምፓላ፣ በመሳሰሉ የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች በምድር ወገብ ፀሐይዋ ማዘቅዘቅ ስትጀምር ሐበሾች ወደ ከፈቷቸው ቡና ቤቶች እና ባሮች ጎራ በሉ። የአብርሃም አፈወርቂን ሙዚቃ እንደሰማችሁ የቴዎድሮስ ካሳሁንን “ኻብ ዳህላክን” ወዲያው ልታደምጡ ትችላላችኹ። ሌላም ዘፈን …፤ “አዲስ አበባ ቤቴ” የሚለውን ዘፈን  ጭምር ሁሉ። እነዚህን ዘፈኖች ሲሰሙ ያስከፈቱትን የላጋር ቢራ ቶሎ ቶሎ የሚጎነጩ …ሲጋራቸውንም በላይ በላዩ የሚያጨሱ ወጣቶች ልትታዘቡ ትችላላችሁ። በሙዚቃው ውስጥ ሕይወታቸውን እያነበቡ ትላንትን፣ ዛሬን እና ነገን እያሰቡ እንደሚኾን አትጠራጠሩ።

ብዙዎች “አምቼ”ዎች እንዲህ ዐይነት ሙዚቃ ሲያደምጡ በትዝታ እና በቁጭት ወደ አዲስ አበባ በሐሳብ መመለሳቸው አይቀርም። በአንዳንዶች ሕሊና ከዐሥር ዓመት በፊት ያዩዋትን አዲስ አበባ በዐይነ ሕሊናቸው ድቅን ትላለች። “አምቼ”ዎች ላደጉባት አዲስ አበባ ልዩ ፍቅር እና ግምት አላቸው። ከአዲስ አበባ የተነጠሉበት መንገድ ደግሞ አዲስ አበባን በበጎ ብቻ እንዳያስታውሷት አድርጓቸዋል። ታዲያ በሐሳብ መናወዛቸውን የሚያናጠብ ጸብ ብዙ ጊዜ አይጠፋም።

ጁባም ኾነ ናይሮቢ፣ ካምፓላም ኾነ ካርቱም ኤርትራውያን እና ኢትዮጵያውያን አብረው የሚታደሙባቸው የምሽት ክበቦች አንዳንድ ጊዜ ጸብ አያጣቸውም። በአንድ ዜማ አብረው ሲደንሱ የነበሩት እና ራሳቸውን “ሀበሻ “ እያሉ የሚጠሩት  ኢትዮጵያውያን እና ኤርትራውያን ከአፍታ ቆይታ በኋላ ሊጣሉ ይችላሉ። “በሀበሾቹ” መካከል ፀብ ከተነሳ “ሰላም አስከባሪዎች” በገላጋይነት ከተፍ ይላሉ። “ጁባ ላይ አምቼዎች  ‘ሰላም አስከባሪዎች’ ተብለው ይታወቃሉ” ይላል ቢኒያም።

በመላው የምሥራቅ አፍሪካ ከተሞች ተበትነው የሚገኙት ከኢትዮጵያውያን እና ከኤርትራውያን ስደተኞች ወገኖቻቸው መሳ ለመሳ የስደት ኑሮቸውን እየገፉ የሚገኙ “አምቼ”ዎች ልክ በመላው ዓለም እንደተበተኑ የስያሜ ተጋሪዎቻቸው ሁሉ እርስ በእርስ ባላቸው ትሥሥር ይታወቃሉ። “I Love being Amiche” በተሰኘው የአምቼዎች ፌስ ቡክ ገጽ ላይ አስተያየቱን የሰጠ አንድ ወጣት እንዲህ ሲል ምኞቱን አስቀመጠ። “አምቼዎች አንድ ላይ የምንኖርበት ዓለም ቢኖረን እንዴት ደስ ባለኝ።”

“አምቼ”ዎች ሕልማቸው በእነርሱ ምኞት ብቻ እንደማይሳካ ያውቁታል። ሥልጣን ላይ ያሉት የፖለቲካ ቡድኖች ለጥያቄዎቻቸው የሚኾን መልስ ይዘዋል። ጉዳዩን ለማየት የሚያስችል ፍፁም ፈቃደኝነት ባይታይባቸውም። ማኅደረ ግን ለማንነት ጥያቄው መፍትሄ ያለው ይመስላል። “ከኢትዮጵያዊነት እና ኤርትራዊነት በላይ የጨርቆስ እና የአባ ሻወል ልጅ መባል ይበልጥብኛል” ይላል። ብዙ አምቼዎች በሚገናኙበት የፌስ ቡክ ገጽ ላይ ሰለሞን ዘርዐይ የሚባል አባል  ይህችን ግጥም አሰፈረ።

ብለነው ብለነው ካልኾነ ነገሩ

አምቼና ዶላር የትም ነው አገሩ።

ዘገባ-  ሱቢ ዓለሙ፣ ማስረሻ ማሞ

ማጣቀሻ ጽሑፎች

1, ERITREA & ETHIOPIA: LARGE-SCALE EXPULSIONS OF POPULATION GROUPS AND OTHER HUMAN RIGHTS VIOLATIONS IN CONNECTION WITH THE ETHIOPIAN-ERITREAN CONFLICT, 1998-2000)

2,Case Material on Ethnic Eritrean Deportees from Ethiopia Concerning Human Rights Violations : The Uprooted

Case Material on Ethnic Eritrean Deportees from Ethiopia   Concerning Human Rights Violations

by Prof. Asmarom Legesse

3, Jennifer Riggan, Ph.D. In Between Nations: EthiopianBorn Eritreans, Conflict and Nationalism  Paper presented at the International Studies Association Annual Meeting New York City, February 1518, 2009

4,

ለዚህ ጽሑፍ አስተያየት በመስጠት የመጀመሪያ ይሁኑ!

Leave a Reply

You must be to post a comment.

የወሲብ መጻሕፍት የገበያ ሃድራ

አንጋፋው ደራሲ ስብኀት ገብረ እግዚአብሔር የጀመረው የ“እንደወረደ” የወሲብ ሥነ-ጽሑፍ ዛሬ ዛሬ ተስፋ የሚጣልባቸው ወጣት ደራሲያን ሳይቀሩ የብእር ስም እየፈጠሩ እንዲገቡበት እያደረጋቸው ነው። ስብኀት በዚህ ርእስ ሥር መጠራት ከሌለባቸው ኾኖም የወሲብ ወላፈን ከነካቸው ድንቅ ሥራዎቹ መሀል አምስት ጊዜ የታተመለት “ሌቱም አይነጋልኝ” እና ሦስት ጊዜ የኅትመት ብርሃን ያገኘለት “ትኩሳት” ይጠቀሳሉ። እነዚህ ወጥ ድርሰቶቹ ያገኙት ተቀባይነት በወሲብ ሥነ-ጽሑፍ የራሳቸውን ተጽዕኖ አልፈጠሩም ለማለት ግን ያዳግታል። ኾነም ቀረ የኢትዮጵያ የኅትመት ታሪክ በኮሎኔሉ አብዮት ተጀምሮ፣ በ“እንደወረደ” የስብኀት መንገድ አሳብሮ ዛሬ የ“ዘ”ዘመን ላይ ደርሷል። የሚያቆመው ያለ እስከማይመስል ድረስ፤ የኀትመት ዋጋ መናርም እንኳ ቢኾን።

This post is available in: ኸንግሊስህ

(ሙሳ ያሲን)

የሙሉ ጊዜ ስመ ጥር ደራሲ ነው። አሳታሚዎች ሰላምታ ካቀረቡለት በኋላ የሚያስከትሉት የሁልጊዜ ምክር ተመሳሳይነት ይገርመዋል። “ጎበዝ ደራሲ ነህ ግን… እንዲህ ብጥስጥስ ያለ ሳንቲም ከምትሰበስብ ለምን ሸጋ የኾነ የወሲብ ሳይኮሎጂ አትጽፍም። ላንተም ለኛም ጥሩ የሚኾነው እርሱ ነው፣ ካንተ ያነሰ ችሎታ ያላቸው ልጆች ይኸው ለገበያ የሚኾን ነገር እየጻፉ ቀድመውህ ሀብታም እየኾኑ ነው፤ እስኪ አስብበት።”

ይህ አሳታሚዎች ለደራሲዎች የሚያቀርቡት አባታዊ ምክር እንደዋዛ የሚታይ አይደለም፡፡ የኅብረተሰባችንን ድብቅ ሥነ-ልቡናዊ ፍላጎት የሚያመላክት ነው። የምክሩ ትርጉም ግን ከዚህም ይዘላል።

የወሲብ ሰልፍ

የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ በ1980ዎቹ አጋማሽ እና መጨረሻ በተለምዶ “ወመዘክር” በሚባለው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ-መጻሕፍት እና ቤተ-መዛግብት የጋዜጣ ክፍል ውስጥ የነበረውን ኹኔታ ፈጽሞ አይዘነጋውም። በጣውላ የታነጸው በቢጫማ ቀለም የተዋበው ክፍል በወቅቱ በአገሪቱ የሚታተሙትን የመንግሥት ኾኑ የግል ጋዜጦችን እና መጽሔቶችን ለጋዜጣው ክፍል ታዳሚ ያቀርብ ነበር። ኾኖም በወቅቱ ይወጡ ከነበሩት የኅትመት ውጤቶች አንባቢው ቀዳሚ ትኩረት ይሰጥ የነበረው እንደ “ጥንቅሽ”፣ “ማዶና”፣ “የፍቅር ማኅደር”፣ “ኤሮቲካ”፣ “እንኮይ” እና “እውነተኛ ፍቅር” ላሉት ወሲብ ተኮር ጋዜጦች እና መጽሔቶች ነበር። በዚሁ ጋዜጣ ክፍል ውስጥ ይታደሙ ከነበሩት መካካል 75 መቶ የሚኾኑት ወሲብ ነክ የኅትመት ውጤቶችን የመኮምኮም ልማድ አዳብረው ነበር። የጋዜጣ ክፍሉ በጊዜ ስለሚሞላ ብዙ አንባቢያን በመጡበት እንዲመለሱ ይገደዱም ነበር። አንዳነድ ደንበኞች ግን እነዚህን የወሲብ ጋዜጦች ለማግኘት በትእግስት ይጠባበቃሉ፤ እየተፋፈሩ። ኹኔታው የወሲብ ፊልምን ለመታደም በአንድ ክፍል እንደመገኘት ዐይነት ስሜት ነበረው።

በወቅቱ “ማዶና” ጋዜጣ የአንዲት ኢትዮጵያዊት ሴትን በእውን ዓለም ይሆናል የማይባል የወሲብ ገድል የሚተርክ “ኢትዮጵያዊቷ ማዶና” የሚል ዐምድ የነበረው ሲኾን የቅንዝረኛዋን ሴት ገድል ከሰማንያ ሳምንት በላይ በጋዜጣው ላይ ተስተናግዷል። ጋዜጣው በወሲብ አራራ በእጅጉ የተለከፈችውን ሴት አንድ ልዩ ገድል በየሳምንቱ ይዞ ይቀርብ ነበር። “ጥንቅሽ” ጋዜጣ በበኩሉ “የሴተኛ አዳሪዋ ገመና” በሚለው ዐምዱ ወጣ ያሉ እና ማኅበረሰቡ ዘንድ ፀያፍ ተደርገው የሚቆጠሩ ወሲባዊ ኹነቶችን ልብን በሚሰቅል እና ለወሲብ በሚያማልል ኹኔታ ያቀርብ ነበር። ለእነዚህ ሁለት ዐምዶች ነበር የወመዘክር ቤተ መጻሕፍት በወሲብ ሲቃ ጡዘት ላይ ትዋልል የነበረው። የጋዜጣው ክፍል ታዳሚዎች እነዚህን ወሲባዊ ትርክቶች ቀድሞ ለማንበብ ብርቱ ትግል ያደርጉ ነበር። ከቤተ መጻሕፍቱ አስተናጋጆች እስከመሻረክ ድረስ። እነዚህ ጋዜጦች ከሌሎች በዚህች ክፍል ይገኙ ከነበሩ ጋዜጦች በተለየ መልኩ ይሟሽሹ ነበር። የሰው እጅና ዐይን ስለሚበዛባቸው።

የሌተናል ኮሌኔሉ መፈንቅለ- ወሲብ

በሕይወት የሌሉት ሌ/ኮሎኔል ጌታቸው መኮንን ሐሰን ከላይ ከተጠቀሱት ወሲብ ተኮር የኅትመት ውጤቶች በዋናዎቹ ውስጥ የመሥራችነት እና የባለቤትነት ሚና ነበራቸው። በ1987 ዓ.ም አካባቢ በርካታ ሴቶች “እንኮይ” መጽሔትን ጨምሮ ሌሎች ወሲብ ነክ ጋዜጦች “ሴቶችን ወሲባዊ ሸቀጥ አድርገው ያቀርባሉ” በሚል “በሴቶች እኩልነት የሚያምነው መንግሥታችን በአሳታሚዎች እና በአዘጋጆች ላይ ሕጋዊ ርምጃ ይውሰድልን” ብለው ሰላማዊ ሰልፍ እስኪወጡ ድረስ ኮሎኔሉ በኢትዮጵያ የጋዜጣ እና የመጽሔት ኅትመት ታሪክ ከፍተኛ ሊባል የሚችል ትርፍ አጋብሰዋል። በወቅቱ ከነበሩት ወሲብ ተኮር ኅትመቶች ከሲሶ በላዩ የሌተናል ኮሌኔሉ ንብረቶች ነበሩ።

ሌ/ኮሎኔል ጌታቸው ከጋዜጦች እና መጽሔት ዕገዳ በኋላም ቢኾን እጃቸውን አጣምረው አልተቀመጡም። በወሲብ ተኮር ጋዜጦቹ እና መጽሔቶቹ የተደረገባቸውን መፈንቅል ለመቀልበስ ወጠኑ። የወሲብ ነክ የኅትመት ውጤቶችን ገበያ እና የኅብረተሰቡን ታማኝ አንባቢነት በዉሉ ያጠኑት ሌ/ኮሎኔሉ ማርሻቸውን ወደ መጻሕፍት ቀየሩት።

ኮሎኔሉ ቀድሞ እጃቸውን ያሟሹባቸውን የነአጋታ ክሪስቲን፣ ሼርሎክ ሆልምስን እና ሌሎችም ዝነኛ ወንጀል ነክ ታሪኮችን ወደ አማርኛ የመተርጉሞን ነገር ለጊዜው ጋብ በማድረግ ፊታቸውን ወደ ወሲብ ዘመም መጻሕፍት አዞሩ።

በመጀመርያ ወደ አማርኛ የተረጎሙት የኸርቪንግ ዋላስን “የደፈረሰ እንባ” ሲኾን መጽሐፉ ዐሥራ አንድ ጊዜ ኅትመት ቤትን ጎብኝቷል። የዚህ መጽሐፍ ሽፋን ከወገቧ በላይ ርቃኗን የኾነች ወጣት በወሲባዊ አቀማመጥ ጡቶቿን ወድራ የምትታይበት ምስል ነበር። የመጽሐፉ ጭብጥ አንዲት ወጣት ሴት ወሲብን እንደምትወድ በሚዲያ ከገለጸች በኋላ በአራት ወንዶች ተጠልፋ ተደጋጋሚ ወሲባዊ ጥቃት ሲደርስባት እና ከዚህ ለማምለጥ የምታደርገውን ብርቱ ትግል ይተርካል። ይህ የትርጉም መጽሐፍ በወቅቱ ብዙ ሺሕ ኮፒ በመሸጥ መነጋገርያ ኾኖ ቆይቷል፡፡

ኮሎኔሉ ከዚህ መጽሐፍ በኋላ የተረጎሟቸው “የባሎች ገመና” እና “የዘቪራ ሆላደርን” ግለታሪክ ናቸው። ዛቬራ ለዚህ ግለ ታሪክ መጽሐፍ የሰጠችው ኦሪጅናል ርእሰ “the happy hooker” ይሰኛል። ከዚህ ሥራ በተጨማሪ “አልሎት” /the bitch/፣ “መንታዋ አነር” /13 at dinner/ እና “ኮርማው” /the stud/ የተሰኙት ወሲብ ተኮር የኾኑት የትርጉም ሥራዎቻቸው በተደጋጋሚ ታትመውላቸዋል። የኮሌኔሉ ሁሉም የትርጉም ሥራዎች ጡት መያዣ እና የውስት ሱሪ ባደረጉ እጅግ አማላይ እና ወሲብ ቀስቃሽ አለባበሶች የተሞሉ ነበሩ። የፊት ገጽ ሽፋኖችን አማላይ አድርጎ የማቅረብን ስልት በስፋት ያስተዋወቁት ኮሎኔሉ እንደኾኑ መጻሕፍት አሳታሚዎችም አሌ ሳይሉ የሚስማሙበት ጉዳይ ነው።

ድኅረ ኮሎኔል

ከኮሎኔሉ መፈንቅለ ወሲብ ቀጥሎ የእርሳቸውን አርዐያ ይዘው የቀጠሉ ብዙ ደራሲዎች እና ተርጓሚዎች ተፈጠሩ። የወሲብ ተኮር መጻሕፍት የገበያ ሃድራ የማያባራ እንደኾነ የተረዱ አያሌ አሳታሚዎች ውጭ አገር የሚሄዱ ነጋዴዎችን እና የበረራ አስተናጋጆችን ወሲባዊ መጻሕፍት እንዲያመጡላቸው በማባበል ሥራ ተጠመዱ። የሚመጡላቸውን መጻሕፍት ገነጣጥሎ ለብዙ ወጣት ተርጓሚዎች በማደል ቶሎ “ለጥብስ” የማድረስ ሥራ ላይ ተሰማሩ። ስኬታማ ለመኾን ችለው ነበር።

በ1994 ዓ.ም ለመጀመርያ ጊዜ ለኅትመት የበቃው “የፍቅር ጥበብ” የተሰኘው መጽሐፍም ቢኾን አሁን 12ኛ ዕትም ላይ ነው ያለው። ይኸው ማኅሌት ጥላሁን በሚል የብእር ስም የተተረጎመው መጽሐፍ ልቅ የወሲብ መጽሐፍ ባይኾንም በርካታ ገጾቹን ለወሲብ ተኮር ጉዳዮች ሰውቷል። በተመሳሳይ የወሲብ ተኮር ሥነ-ጽሑፍ ላይ የተሰማሩ አሳታሚዎች እና አስተርጓሚዎች እንደሚያምኑት የትኛውም የፖለቲካም ኾነ የታሪክ መጽሐፍ እንደ ወሲብ ተኮር መጻሕፍት ሰፊ ገበያን ማሸነፍ አልቻሉም።

የ“ዘ” ዘመን

የካዛንቺስ ሴተኛ አዳሪዎች እና የደንበኞቻቸውን ግንኙነት በተዋንያኑ ልቅ ቋንቋ የሚተርክው “መኀልየ መኀልየ ዘ-ካዛንቺስ” ለኅትመት ገብቶ ለገበያ በቀረበ ጊዜ በኅትመት ሚዲያዎች ዘንድ ከፍተኛ ውዝግብን አስነስቶ ነበር። መጽሐፉ በፊት ገጹ ላይ “ከ17 ዓመት በታች የኾኑ ሰዎች እንዲያነቡት አልተፈቀደም” የሚል ማስገንዘብያ ቢኖረውም በልቅ የቋንቋ አጠቃቀሙ ከፍተኛ ውግዘት ገጥሞት ነበር። መጽሐፉ ከልማዳዊው የማኅበረሰቡ የወሲብ አመለካከት የሰማይ ያህል የራቁ፣ ያፈነገጡ እና የተቃረኑ የካዛንቺስ የሌሊት የወሲብ ገጠመኞችን በካዛንቺስኛ የቡና ቤታ ቋንቋ ይተርካል። በቶሎ ከገበያ እያለቀ አሁን 6ኛ ዕትሙ ላይ ደርሷል። አሳታሚዋ ስንዱ አበበ “የአገራችን ወጣት በኤድስ እየተቀጠፈ ያለው ግልጽነት በማጣቱ ነው” የሚል ይዘት ያለው የሞራል ማለዘቢያ በመጽሐፉ መግቢያ ላይ የጻፈችበት ቢኾንም ውዝግቡን ለማብረድ በቂ ማስተባበያ ኾኖ አልተገኘም። ውዝግብ ለመጽሐፍ ገበያ የማቀጣጠያ አንዱ ስልት መኾኑን የሚያውቁ የመጽሐፍ አከፋፋዮች ይህን ፈር ቀዳጅ መጽሐፍ በብዛት ሸጠዋል። አሁንም ድረስ መጽሐፉ በገበያ ላይ በቀላሉ አይገኝም።

በአዲስ አበባ ውስጥ የገዘፈ ስም ካላቸው መጻሕፍት አከፋፋይ መደብር ባለቤት ከኾኑት አንዱ እንደሚሉት የአሳታሚዋ የስንዱ አበበ ቸልተኝነት እና ስንፍና እንጂ መጽሐፉ እስከአሁን ከዐሥር ዕትም በላይ መሄድ ይችል ነበር። “ይህ ሥራ ያለውን ሰፊ ተቀባይነት ስለማውቅ ሙሉ የኅትመት ወጪውን እኔ እንድሸፍን ጠይቄ ምላሽ አላገኘሁም” ይላሉ እኒሁ አሳታሚ። ውልደቱ እና እድገቱ ካዛንቺስ የኾነው የመጽሐፉ ደራሲ ተድባበ ጥላሁን  ይህንኑ ሥራውን ከአመርቂ ክፍያ ጋራ ወደ ፈረንሳይኛ ቋንቋ መመለሱ ይታወቃል።

የዚህን የ“ዘ”ዘመን መሥራች ወሲብ ሙሊት ሥራ ስኬት የተረዱ አሳታሚዎች የደራሲ ያለህ ማለት ጀመሩ። በዚህም የ“ዘ” ዘመን መጀመር ታወጀ።

የቼቺንያን የሌሊት ግብር በቺቺንያ ወሲብ ሸማች ደንበኞች ልቅ ቋንቋ የሚተርከው እና በደረጄ አያሌው የተጻፈው “መኀልየ መኀልየ ዘ ቼቺኒያ” የወሲብ ገበያው ውስጥ ለመግባት የመጀመርያው ነበር። በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥ አሁን አራተኛ ዕትም ላይ እንደደረሰ ለአሳታሚው ቅርብ የኾኑ ምንጮች ይገልጻሉ። መጽሐፉ የሰፈሩን የወሲብ ንግድ ተዳዳሪዎች አስከፊ ገጽታ በጥልቀት ለማሳየት ይሞክራል።

የዚህን መጽሐፍ ስኬት ተከትሎ ከጥቂት ወራት በኋላ ለገበያ የቀረበው እና ትኩረቱን በተመሳሳይ መቼት ላይ ያደረገው “የቺቺኒያ ምስጢራዊ ሌሊቶች” የተሰኘው መጽሐፍ አሁን ሦስተኛ ዕትም ላይ ደርሷል። የዚህ መጽሐፍ ባለታሪኮች ጥቂት ቢኾኑም በሤራ አወቃቀር፣ በገፀ-ባሕርይ አሳሳል እና በሥነ-ጽሑፋዊ ዉበቱ ሲመዘን ይህ መጽሐፍ ከሁሉም ወሲብ ተኮር መጻሕፍት የላቀ እንደኾነ የሚናገሩ ጥቂት አይደሉም።

ባሳለፍነው ክረምት ለገበያ የቀረበው እና በጋዜጠኛ ሚልዮን ሹሩቤ የተጻፈው “ወሲባዊ ውስልትና ዘ አዲስ አበባ” የተሰኘው መጽሐፍ የመጀመርያ ዕትም በአከፋፋዮች ዘንድ ያለቀው ዐሥር ቀናት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ነበር። ይህ መጽሐፍ እስከ አሁን ከጠቀስናቸው በተቃራኒ መልኩ የሚተርከው ስለ ቤት ልጆች እና ባለትዳሮች ወሲባዊ ሕይወት ነው። መጽሐፉ አሁን ሁለተኛ ዕትሙ እየተሸጠ ይገኛል። ደራሲው ከሚተርካቸው እውነታዎች በተጨማሪ ከበርካታ የቤት ልጆች እና ባለትዳሮች ጋራ በቴፕ የተቀረጸ ቃለ-መጠይቅ አድርጓል።

ወሲብ ያበላል

ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ ለገበያ ከቀረቡ የወሲብ ሥነ-ልቡና መጻሕፍት በአመዛኙ ኤሮቲክ ፊልሞች እንዲመስሉ አድርጎ ማቅረብ ተጨማሪ ገበያን እንደመፍጠር እየታየ ነው። በጨዋ ቃላት እና መንገድ ወሲብን ማውራት በአዋጅ የታገደ ይመስል የብዙዎቹ መጻሕፍት አፈጣጠር ልቅነት ይታይበታል። ይህም ከልባሳቸው ይጀምራል። ፈረንጅ ሴት ሞዴሎች ጡቶቻቸውን ወድረው የሚታዩባቸው መጻሕፍትን ቁጥር ሼልፍ ይቁጠረው።

በቅርብ ጊዜ በትርጉም ሥራዎች ደረጃ ያሉትን እንኳ ብንቆጥር ከ20 በላይ እንሄዳለን። ከኒኮል ቤላንድ “the girl next door” የሚለው መጽሐፍ “የሴቶች ገመና’ በሚል ርእስ ወደ አማርኛ ከተመለሰ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ስምንተኛ ዕትም ላይ ደርሷል። የዚህ መጽሐፍ ቋሚ ደንበኞች የሁለቱም ፆታ አባላት ናቸው። የጆን ግሬይ “Mars and Venus in the Bedroom” የተሰኘው መጽሐፍ “የወሲብ ጥበብ” በሚል ርእስ በመዓዛ ቴዎድሮስ ወደ አማርኛ የተተረጎመ ሲኾን ገና መንፈቅ ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሦስተኛ ዕትም ደርሷል፡፡

በኢትዮ ቻናል ጋዜጣ ላይ ሰዓት እላፊ በሚለው “ተወዳጅ” ዐምድ ሥር ለአንድ ዓመት የቀረቡትን የአዲስ አበባ ሴተኛ አዳሪዎችን ሕይወት የሚዳስሱ ስብስቦች “ሰዓት እላፊ” በሚል ርእስ በመጽሐፍ ያሳተመው የዐምዱ አዘጋጅ ኤርምያስ ስዩምም ገበያው ሰምሮለታል። ጋዜጣው በሁለት እግሩ እንዲቆም ያስቻለውም ይኸው ዐምዱ እንደኾነ የሚናገሩ ብዙ ናቸው።

አንጋፋው ደራሲ ስብኀት ገብረ እግዚአብሔር የጀመረው የ“እንደወረደ” የወሲብ ሥነ-ጽሑፍ ዛሬ ዛሬ ተስፋ የሚጣልባቸው ወጣት ደራሲያን ሳይቀሩ የብእር ስም እየፈጠሩ እንዲገቡበት እያደረጋቸው ነው። ስብኀት በዚህ ርእስ ሥር መጠራት ከሌለባቸው ኾኖም የወሲብ ወላፈን ከነካቸው ድንቅ ሥራዎቹ መሀል አምስት ጊዜ የታተመለት “ሌቱም አይነጋልኝ” እና ሦስት ጊዜ የኅትመት ብርሃን ያገኘለት “ትኩሳት” ይጠቀሳሉ። እነዚህ ወጥ ድርሰቶቹ ያገኙት ተቀባይነት በወሲብ ሥነ-ጽሑፍ የራሳቸውን ተጽዕኖ አልፈጠሩም ለማለት ግን ያዳግታል። ኾነም ቀረ የኢትዮጵያ የኅትመት ታሪክ በኮሎኔሉ አብዮት ተጀምሮ፣ በ“እንደወረደ” የስብኀት መንገድ አሳብሮ ዛሬ የ“ዘ”ዘመን ላይ ደርሷል። የሚያቆመው ያለ እስከማይመስል ድረስ፤ የኀትመት ዋጋ መናርም እንኳ ቢኾን።

ለዚህ ጽሑፍ አስተያየት በመስጠት የመጀመሪያ ይሁኑ!

Leave a Reply

You must be to post a comment.

[አንድ ለቅዳሜ ] ሥልጣን እንጂ ተጠያቂነት የሌለበት “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ”

ኢሕአዴግ የምርጫ 2002 እፍረቱን ለማረሳሳት (ሊረሳ የሚችል ከሆነ) ብዙ ሙከራዎችን ማድረግ ነበረበት። የመጀመሪያው እና ትልቁም “የእድገት እና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ” ተብሎ የቀረበው ሰነድ ነው። ዕቅዱ በይዘቱም ሆነ በቅርጹ ሰፊ የሐሳብ ልውውጥን የሚጋብዝ ነው። እስካሁን በብዛት ትኩረት የተሰጠው ግን ዕቅዱ ሊሳካ የሚችል በመሆኑና ባለመሆኑ ላይ ነው። ዕቅዱ የሚሳካም ይሁን አለዚያም የማይፈጸም፣ የሰነዱ ፖለቲካዊ ፋይዳ ተገቢውን ትኩረት ያገኘ አልመሰለኝም። እንደ ሁልጊዜውም እጅ እጅ የሚለው ፕሮፓጋንዳም ብዙዎች ሰነዱን ጨርሶ ማንበብ ቀርቶ ወሬውንም ለመጥላት እንዲቸኩሉ አድርጓል። ሆኖም ዕቅዱ ወደድነውም ጠላነው የአገሪቱን ሕይወት በተለያየ መልኩ የሚነካ እንደመሆኑ መገለል ሳይሆን በጥልቀት መተቸት ይገባዋል እላለሁ።

This post is available in: ኸንግሊስህ

ኢሕአዴግ የምርጫ 2002 እፍረቱን ለማረሳሳት (ሊረሳ የሚችል ከሆነ) ብዙ ሙከራዎችን ማድረግ ነበረበት። የመጀመሪያው እና ትልቁም “የእድገት እና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ” ተብሎ የቀረበው ሰነድ ነው። ዕቅዱ በይዘቱም ሆነ በቅርጹ ሰፊ የሐሳብ ልውውጥን የሚጋብዝ ነው። እስካሁን በብዛት ትኩረት የተሰጠው ግን ዕቅዱ ሊሳካ የሚችል በመሆኑና ባለመሆኑ ላይ ነው። ዕቅዱ የሚሳካም ይሁን አለዚያም የማይፈጸም፣ የሰነዱ ፖለቲካዊ ፋይዳ ተገቢውን ትኩረት ያገኘ አልመሰለኝም። እንደ ሁልጊዜውም እጅ እጅ የሚለው ፕሮፓጋንዳም ብዙዎች ሰነዱን ጨርሶ ማንበብ ቀርቶ ወሬውንም ለመጥላት እንዲቸኩሉ አድርጓል። ሆኖም ዕቅዱ ወደድነውም ጠላነው የአገሪቱን ሕይወት በተለያየ መልኩ የሚነካ እንደመሆኑ መገለል ሳይሆን በጥልቀት መተቸት ይገባዋል እላለሁ።

በዚህ አጭር ጽሑፍ ልመልሳቸው እንደማልችል ባውቅም ጥቂት ጥያቄዎችን ልሰንዝር። ጥያቄዎቹ የውይይቱን ፈር ከማሳየት አልፈው ቀያጅ እንዳይሆኑ ምኞቴ ነው።

1. ዕቅዱ 2020ን (እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር) እንደ መዳረሻው ታሳቢ ያደርጋል። ሰነዱ እንዲያውም ያለፉትን አምስት ዓመታትም (1997-2002) የዚሁ የረጅም ዘመን (ከ1997-2020 ያሉትን 24 ዓመታት) ዕቅድ “የመጀመሪያ አምስት ዓመት” ብሎ ይጠራል። እንዲህ ያለ የ24 ዓመት (በማጠጋጋት የሩብ ክፍለ ዘመን እንበለው) አገራዊ የልማት ዕቅድ እንዳለ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያውቃልን? ምነው ዕቅዱ መኖሩ እና መጀመሩ ሳይበሰር ሁለተኛው የአምስት ዓመት ዕቅድ እንዲህ ተወራለት? ኢሕአዴግ ለምን የረጅም ዘመን ዕቅድ ኖረህ ተብሎ አይወቀስም፤ ይመሰገናል እንጂ። ጥያቄው ወዲህ ነው።

    እንደ ኢትዮጵያ ከድህነት የመውጫውን ወሳኝ የመጀመሪያ ርምጃ የመራመድ ሸክም ላለባቸው አገሮች ይህን መሰል ዕቅዶች ቢሳኩም ኾነ ቢከሽፉ ውጤታቸው ለብዙው ዜጋ የሚተርፍ ነው። ስለዚህ እንደ ቻይና የሚልዮኖችን ሕይወት ለመገበር የሚፈቅድ “አብዮተኛ” አመራርን አና አመለካከትን የሚታገስ ታሪካዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎች መሟላት አለባቸው፤ አለዚያ ደግሞ ቢያንስ ዋና ዋና ፍላጎቶችን የሚወክሉ ቡድኖች ሌላው ቢቀር በመሠረታዊ ጭብጦችና ግቦች ላይ ሊመክሩበትና ሊስማሙበት የሚችሉበትን ከባቢ መፍጠር ያስፈልጋል።

    ለየዋህ ተመልካች ኢሕአዴግ ሁለቱንም ጽንፎች (የማኦንም ሆነ የአገራዊ መግባባትን መንገድ) ያልመረጠ ይመስላል። ላይ ላዩን ስለ ብሔራዊ መግባባት ቢሰብክም ይህን የ25 ዓመታት አገራዊ ዕቅድ መተግበር ሲጀምር ለስሙ እንኳን ሰፊ የውይይት መድረክ (ድርጅቱ የሌሎችን ሐሳብ ፈጽሞ የማያስተናግድ ከመሆኑ አንጻር ውይይቱን ድራማ ልንለው እንችላለን) መጥራት አላስፈለገውም። እርግጥ አሁን “የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት” በሚል የሰበሰባቸውን ካብ አይገባ ድንጋይ የሆኑ ፓርቲዎች ሰብስቦ በዕቅዱ ላይ አስተያየት ስጡ ብሎ ሲጋብዛቸው ታይቷል። እንግዲህ በቃ አገር መከረበት ማለት ነው። በተቃራኒው ግን ኢሕአዴግ የማኦን (የቻይናን) አርአያ በመከተል ቁም ነገር ያለው ተቃራኒ ሐሳብ ሊያቀርቡ የሚችሉ ግለሰቦችን፣ ብድኖችን እና ማኅበራዊ/ሲቪል ተቋማት የሚያገል፣ የሚያርቅ እና ባስ ሲልም የሚያጠፋ ስልት ቀይሶ ተግባር ላይ አውሏል።

    የዕቅዱ ስኬት አንድም በጉልበት በመፈጸሙ ከሚያስከፍለው ፈርጀ ብዙ ዋጋ፣ አለዚያም ወሳኝ ፍላጎቶችን የሚያስማማ መሠረት በማጣቱ/በማግኘቱ ከሚከተለው ውጤት ጋራ መያያዙ የግድ ነው። ዕቅዱ የማን ነው? የኢሕአዴግ፣ የመንግሥት፣ የአገር/የሕዝብ…? በ1997 ምርጫ ማግስት ይህን የሩብ ምዕተ ዓመት ዕቅድ አጽድቀው መተግበር መጀመራቸውን እየነገሩን ነው። እንዴት ያለ ድንቅ የጊዜ አመራረጥ ነው? በተለይ ብሔራዊ መግባባት ለሚያሻው ይህን መሰል ዕቅድ! በድጋሚ ዕቅዱ የማን ነው?

    ይህን መሰል አገራዊ እቅዶች ተራ የቁጥር ግብ በማስቀመጥ የሚጠናቀቁ አይደሉም። ከዚያ በፊት ልንፈጥረው የምንፈልገው ማኅበረሰብ ምንነት/ማንነት ከታሪኩና ከተጨባጭ ሁኔታው በመነሳት መተንተኑን ይጠይቃል። ትምህርት ማስፋፋት አንድ ጥሩ ጉዳይ ነው፤ ግን የትምህርቱን ይዘትና ግብ መወሰን በመጨረሻ የፖለቲካ ውሳኔ መሆኑ ባይካሄድም የካድሬ ጨዋታም አይደለም። ለምሳሌ ስለ ትምህርት ጥራት ብዙ ይባላል። አሁን ደግሞ 70/30 የሚለው ሐሳብን መጥቷል። ለመሆኑ ይህ ሁሉ ሐሳብ ትምህርታችን አገራዊ ስር የለውም፤ ወደ ስሩ መመለስ አለበት የሚለውን ጥያቄ ተመልክቶታል? እንግዲህ የረጅም ዘመን አገራዊ ዕቅድ ሲነደፍ እንዲህ አይነት መሠረታዊ ጥያቄዎች ባይመለሱ እንኳን መነሣት አለባቸው ለማለት ነው። በድጋሚ ዕቅዱ የማን ነው?

    2.የዕቅዱ ውጤት ምን ሊሆን ይችላል? ይህ “ዕቅዱ ሊሳካ ይችላል አይችልም?” ከሚለው ጠባብ ጥያቄ በመሠረቱ የተለየና የበለጠም አስፈላጊ ይመስለኛል። ዕቅዱ በወሳኝ መልኩ (ከ70 በመቶ ባላነሰ) ተሳካ እንበል። ይህ ለአገሪቱ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ሕይወት ምን ማለት ነው? በተቃራኒው ዕቅዱ ሳይሳካ ቢቀርስ ምን አገራዊ ጣጣ ያመጣል? ጣጣው ወዴት ሊወስደን ይችላል?

    3. ዕቅዱ የሩብ ምዕተ ዓመት የመሆኑን ያህል የአገሪቱን ሁለንተናዊ ሕይወት የሚያካትት አይደለም። እርግጥ ይህ በኢኮኖሚ ልማቱ ላይ ያተኮረ ሆኖ ሌሎች አጠቃላዩን ስእል የተሟላ የሚያደርጉ ተጓዳኝ እቅዶች አሉ ወይም በዝርዝር ይመጣሉ ከተባለ ጥያቄው ሌላ ይሆናል። 167 ገጾች ያሉትን ይህን ሰነድ ሳነብ የታዘብኩት አንድ ቁም ነገር ጸሐፊዎቹ ርእይ (ቪዥንን) ከዕቅድ (ፕላን) ጋራ የማምታታት ችግር እንደተጠናወታቸው ነው። ሰነዱ በአመዛኙ በቁሳዊ ልማት ላይ ያተኮረ ነው። ዕቅዱ በውጤቱም ሆነ በአፈጻጸም ሒደቱ በአገሪቱ “መንፈሳዊ/ባህላዊ” ሕይወት ላይ የሚያስከትለው ተጽእኖ ምንድን ሊሆን ይችላል?

    4. የዚህ “አገራዊ ዕቅድ” ሰነድ አደገኛ ድክመት አንዳችም የተጠያቂነት መርህ የሚያነሳ አለመሆኑ ነው። በአንድ በኩል ዕቅዱ ቁልፍ ባለጉዳዮች ተሳትፈውበት የተቀረጸ ባለመሆኑ “አገራዊ” ለመባል ያለው እድል የተመናመነ ነው። ይህም ዕቅዱን የኢሕአዴግ ብቻ ያደርገዋል። አስቂኙ ነገር ሰነዱም ሆነ የሰነዱ ባለቤት የሆነው ኢሕአዴግ በአገሪቱን ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ ሊፈጥር የሚችለውን ይህን ዕቅድ ለመፈጸም ያስችላል ያለውን ሥልጣን እና ሀብት ሁሉ እንደተፈቀደ ሲቆጥር አንድም የተጠያቂነት ልጓም አያበጅም።

          ለመሆኑ ይህ ዕቅድ ባይሳካ ተጠያቂ የሚሆነው ማነው? ለምሳሌ ኢሕአዴግ በሥልጣን ላይ ያለው በምርጫ አሸንፎ ነው እንበል። አሁን ያቀረበልንን ዕቅድ ማሳካት ቢሳነው ለባከነው ጊዜ፣ ሀብት ወዘተ ተጠያቂ ይሆናል? ተጠያቂ የሚሆንበት አሠራር አለ? ወይስ እስከዛሬ እንደሚደረገው ምን እንዳልተፈጠረ ተቆጥሮ ስለተገኘው ድል ብቻ እየተዘመረ ሌላ ዕቅድ ይቀርባል?

          ሰነዱ የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር እና የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ኤጀንሲ የተለመደ ግምገማቸውን እንደሚሠሩ ከማተት በቀር የዕቅዱን አፈጻጸም የሚገመግም ገለልተኛ አካል እንደሚኖር አይጠቁምም። ይህ ማለት ኢሕአዴግ ራሱ ያወጣውን ፈተና፣ ራሱ መልሶ፣ ራሱ ነጥብ ሰጥቶ፣ ራሱን ይሸልማል እንደማለት ነው።

          5. በመጨረሻ አንድ የዋሕ ጥያቄ፤ የሰነዱ ደራሲ(ዎች) (እነ)ማን ናቸው? ይህን ማወቅ ስለሰነዱ ብዙ የሚነግረን ነገር ይኖራል። ሰነዱ ምን አይነት ውይይት እንደሚመጥነውም በቀላሉ ለመወሰን ያግዛል። ከጅምሩ የአዘጋጆቹ ማንነት እንደ አገር ምሥጢር የተያዘለት ዕቅድ አፈጻጸሙ ግልጽነት እና ተጠያቂነትን ይላበሳል ብሎ ማመን እንዴት መታደል ነው?!

            በነገራችን ላይ

            ቢቢሲ ለረሃብተኞች የተሰበሰበ ገንዘብ “ለመሣሪያ መግዣ ውሏል” በማለት ባቀረበው ዘገባ የተሳሳተ ትርጉም/ስሜት በሚሰጥ መልኩ ስሙ ተነስቷል ያለውን ባንድ ኤድ እና መስራቹን ቦብ ግለዶፍን ይቅርታ ጠይቋል። ታዲያ ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥትም እኔም ይቅርታ መጠየቅ አለብኝ ሲል መግለጫ አውጥቷል። አልፎም ቢቢሲ ብቻ ሳይሆን ሒዩማን ራይትስ ዎችን (ኤች.አር.ደብሊው) የመሳሰሉ ስሙን በክፉ የሚያነሱ ሁሉ ይቅርታ እንዲጠይቁት ተማጽኗል፣ አሳስቧል።

            ዓመቱ መንግሥት ይቅርታ እየተጠየቀ እርሱም ይቅርታ እየሰጠ የሚያልፍበት ሊሆን ነው ማለት ነው። ግን የኢትዮጵያ መንግሥት መግለጫ አንድ ነገር በአባሪነት አያይዞ መላክ ነበረበት፤ ይቅርታ ጠያቂዎቹ ቢቢሲ እና ኤች.አር.ደብሊው የሚፈርሙበትን የይቅርታ ደብዳቤ አርቅቆ መላክ ነበረበት።

            የቢቢሲው የአፍሪካ ኤዲተር ማርቲን ፕላውት እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ድርጅት ሐላፊዎች/ሪፖርት ጸሐፊዎች የሚፈርሙት የይቅርታ መጠየቂያ ደብዳቤ ምን እንደሚል መገመት መቼም ቀላል ነው። ይቅር ባዩ መንግሥታችን! ዓለም ሁሉ አጥፊ እና ይቅርታ ጠያቂ፤ አንተ ደግሞ ጻድቅ እና ይቅርታ ሰጪ ነህ።

            One Response to “[አንድ ለቅዳሜ ] ሥልጣን እንጂ ተጠያቂነት የሌለበት “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ””

            1. WEHA BEWKTUT EMOCHEEEE…..

            2. This news is intended to give the impression to the readers that the rhetoric of economic development is ridiculous.
              Just out of curiosity, has anyone ever seen any positive news about Ethiopia on ANO?

            3. man neber kahun behuala etiban yemibal neger anteyikim yalew_….tiyake milikit ….

            Leave a Reply

            You must be to post a comment.

            Bad Behavior has blocked 564 access attempts in the last 7 days.