አገቱኒ በመሥፍን መንፈሳዊ
ፕሮፌሰር ምን ማለታቸው እንደኾነ ባያብራሩትም የመጽሐፋቸው ርዕስ ያደረጉትን ቃል ከመዝሙረ ዳዊት የወሰዱት ይመስላል። “አገቱኒ” የሚለው የግእዝ ቃል “ከበቡኝ” የሚል ትርጉም ሲኖረው፤ በቤተክርስቲያን ሥርዓት የስቅለት ዕለት ከሚዘመሩ መዝሙሮች መካከል አንዱ ነው። የመዝሙሩም አንዱ አርኬ “አገቱኒ ከለባት ብዙኃት” ይላል ትርጉሙም “ብዙ ውሾች ከበቡኝ” ተብሎ በ1953 ዓም የአማርኛ ትርጉም ላይ ተተርጉሟል። ይህም መዝሙር የኢየሱስ ክርስቶስን የሞት ጣዕር እንደሚገልጽ በጥንታዊው የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ይታመናል። ፕሮፌሰርን የከበቧቸው እነማን ናቸው? በርዕሱ ሊያስተላልፉት የፈለጉት መልእክት ምንድነው? የሚሉት አይቀሬ ጥያቄዎች በፕሮፌሰር አልተመለሱም።
“ለምን እንደኾነ እንጃ ‘ማፈር ደኅና ሰንብት’ የሚለው ዘፈን ትዝ አለኝ “ ይህች ዐረፍተ ነገር ከፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም አንደበት የፈለቀችው በምርጫ 97 የምርጫ ክርክር ወቅት ነበር። “ገዢው ፓርቲ የአፈጻጸም ብቻ ሳይኾን የአሰማም ችግርም አለበት”፣ “የአገዛዝ መሠረቱ ሕገ አራዊት ነው”። የምርጫ 97 የፖለቲካ ፓርቲዎች ክርክር ሲነሳ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም እንዳይረሱ ካደረጓቸው ንግግሮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው። እነዚሁ ንግግሮቻቸው እየተመነዘሩም ለውዝግብ ከዚያም አልፈው ለእስር ዳርገዋቸዋል። ዛሬም ፕሮፌሰሩ ምን ይናገሩ ይኾን ተብለው የሚጠበቁ ሰው ናቸው። “አገቱኒ ተምረን ወጣን” የተሰኘውም ሥራቸው በዚሁ ጉጉት የሚነበብ መጽሐፍ ነው።
ውስጥ 12 ምዕራፎችን ይዛለች። ሁለተኛውም የመጽሐፉ ክፍል ጸሐፊው በተለያዩ ጊዜያት በጋዜጦች እና በመጽሔቶች ያሳተሟቸው አምሥት ጽሑፎች ተካተውበታል። ከእነዚህም መካከል ፕሮፌሰር ራሳቸውን ከቅንጅት ምክር ቤት ሲያገሉ ለምክር ቤቱ የጻፉት ደብዳቤም በአባሪነት ይገኝበታል።
ፕሮፌሰር ምን ማለታቸው እንደኾነ ባያብራሩትም የመጽሐፋቸው ርዕስ ያደረጉትን ቃል ከመዝሙረ ዳዊት የወሰዱት ይመስላል። “አገቱኒ” የሚለው የግእዝ ቃል “ከበቡኝ” የሚል ትርጉም ሲኖረው፤ በቤተክርስቲያን ሥርዓት የስቅለት ዕለት ከሚዘመሩ መዝሙሮች መካከል አንዱ ነው። የመዝሙሩም አንዱ አርኬ “አገቱኒ ከለባት ብዙኃት” ይላል ትርጉሙም “ብዙ ውሾች ከበቡኝ” ተብሎ በ1953 ዓም የአማርኛ ትርጉም ላይ ተተርጉሟል። ይህም መዝሙር የኢየሱስ ክርስቶስን የሞት ጣዕር እንደሚገልጽ በጥንታዊው የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ይታመናል። ፕሮፌሰርን የከበቧቸው እነማን ናቸው? በርዕሱ ሊያስተላልፉት የፈለጉት መልእክት ምንድነው? የሚሉት አይቀሬ ጥያቄዎች በፕሮፌሰር አልተመለሱም። አንባቢ የራሱን ግምት እንዲወስድ የተተወም ይመስላል።
የፕሮፌሰር መሥፍን “አገቱኒ” አብዛኛው ክፍል ያንጸባረቀው ደራሲው ስለሥልጣን ያላቸውን አመለካከት ነው። “እንደመቅድም፡ እኔ እና ሥልጣን” ከሚለው መግቢያቸው ጀምሮ ፕሮፌሰር ከልጅነት እስከ ዕውቀት ከሥልጣን ጋር የነበራቸውን ተጋድሎ አሳይተዋል። በልጅነት የቄስ ትምህርት ቤትን ሥልጣን ሳይቀር ከሥልጣን ትዝታቸው አንዱ አድርገው ይጠቅሱታል።
“አስተማሪዬ (አለቃ ታምራት የሚባሉ ጎንደሬ ነበሩ) ከአለቆቹ አንዱ አደረጉኝ፤ በመጀመሪያ ስልጣን የቀመስኩት በዚህ ነው፤ ጣመኝ፤ አንድ ተማሪ ‘ጸ’ ስለው ‘ሰ’ ያለ እንደሆነ ጆሮው እስቲቀላ ማሸት አንዱ የሥልጣን መገለጫ ነበረ። በዚያ ላይ አለንጋ ወይም አርጩሜ አለ፤ የመጀመሪያ ደረጃ በሥልጣን የመባለግ ትምህርት ነበር!” ይላሉ ፕሮፌሰር።
በሥራ ዓለም በነበሩበት ሁሉ ያጋጠማቸውን ከሥልጣን ጋር መፋጠጥም ከአንድ አስፈሪ ጥፍራም ጭራቅ ጋር ግብ ግብ የመግጠም ያህል ይተርኩታል። “ወርቅነህ ገበየሁ ያመጣብኝ ጣጣ” ይሉታል ከካርታ ሥራ ድርጅት ወደ ጸጥታ መሥሪያ ቤት መዛወራቸውን ሲገልጹ:፡ ለቀረበላቸውም የሹመት ጥያቄም ምላሻቸው “የምትፈልገው ሬሳዬን ከሆነ አሁኑኑ አድርገው” ሲሉ ተቃውሟቸውን ያቀርባሉ። ሌላም የዚሁ አስፈሪ ሥልጣን ትዝታ አላቸው በዩነቨርሲቲ ኮሌጅ የክፍል ኃላፊ የኾኑት “በመከራ ሰው ጠፍቶ” እንደነበረ ያስታውሳሉ። ያንንም ቢኾን ግን ፕሮፌሰር “በዲሞክራሲያዊ መንገድ” “እንደተገላገሉት” ይገልጻሉ።
ራስ አንዳርጋቸው የአገር ግዛት ሚኒስቴር በነበሩ ጊዜ ረዳት ወይም ምክትል ሚኒስትራቸው እንዲኾኑ በጠየቋቸው ጊዜ የሰጧቸው ምላሽ እንደሚያሳፍራቸው ይገልጻሉ ፕሮፌሰር “የለም እንጣላለን” ለሥልጣኑ ያላቸውን ፍርሃት ገልጸዋል። ሳይፈልጉትም አንድ ወቅት በቅጣት መልክ “የጊሚራ አውራጃ ገዢ” ሌላ ጊዜ ደግሞ “የጊምቢ አውራጃ አስተዳዳሪ” መባላቸውን ያስታውሳሉ። መጨረሻውንም ሲገልጹ “ከመጨረሻው ልጅ ካሣ ወልደማርያም መከተልኝ እና አዳነኝ በሁለተኛው እንደካሣ ወልደማርያም የሚመክትልኝ ሳይሆን አሳልፎ የሰጠኝ አክሊሉ ሀብቴ ነበር” ይላሉ።
በመርማሪ ኮሚሲዮን ውስጥ የነበሩበትንም ጊዜ ሲያስታውሱ “በሕይወቴ በሥልጣን ላይ ላሉ ሰዎች ቅርብ የሆንኩት የመርማሪ ኮሚሲዮን ሊቀመንበር በነበርኩበት አጭር ጊዜ ውስጥ ነው፤ ከማናቸውም ጊዜ ይልቅ ሥልጣን በጥፍሩ ይዞ ሊጎትተኝ የነበረበት ወቅት” እንደነበር ያስታውሳሉ። በማምለጣቸውም እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ። ከዚያም በኋላ የቀረቡላቸውን ሥልጣን ነክ ጥያቄዎች እንዴት እንደመለሱ በመጽሐፋቸው ጠቅሰዋል።
ፕሮፌሰር መሥፍን ከፍቅረ ሥልጣን በተጨማሪ ፍቅረ ነዋይንም እንዴት እንደሚጠየፉት ይናገራሉ። በአንድ ወቅት በልባቸው በድንገት ተጸንሶ የነበረውን መሬት የመግዛት እና ቤት የመሥራት ምኞት ከሥልጣን የማምለጥን ያህል እንዴት እንዳመለጡት ያስረዳሉ።
መጽሐፉ ጸሐፊው ስለራሳቸው የልጅነት እና የሥራ ሕይወት በመጠኑም ቢኾን የገለጹበት ከመኾኑ ባሻገር፤ በ1997 ዓም ምርጫ ላይም የበኩላቸው ያሉበትን ሰፊ ክፍልም አካቷል። ከምርጫ 97 በፊት በኢትዮጵያ የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች የነበሩበት ኹኔታ ምን ይመስል እንደነበረ፣ የቅንጅት መመስረት እና ባህርያቱ፣ የምርጫው ቅስቀሳ እና ምርጫው ከነውጤቱ የነበረበትን ኹኔታ ፕሮፌሰር ዳሰውታል። እርሳቸው እና ሌሎች የቅንጅት አመራር አባላት የታሰሩበትን ሁኔታ እና የፍርድ ሒደቱን አሳዛኝነት አሳይተውበታል። እስረኞቹን የቅንጅት አመራር አባላት እና መንግሥትን ለማስታረቅ ጥረት ያደርጉ የነበሩትን ሽማግሌዎች እንዲሁም የእርቁ ሒደት በይቅርታ መጠየቅ እና ምህረትን በማግኘት ስም የተጠናቀቀበትን ታሪክ በዝርዝር አሳይተዋል። ከመጽሐፉ ይዘቶችም ሁሉ የአንባብያንን ትኩረት ሊስብ የሚችለው ይኸው በፍርድ ቤቱ የነበረውን ኹኔታ እና ሽምግልናውን በጠያቂ (critical) አስተያየት ያዩበት ክፍል ነው።
ለቅንጅት መፍረስ ተጠያቂ የኾነው ማን እንደኾነም ለማሳየት ሞክረዋል። በፕሮፌሰር መሥፍን አስተያየት ለቅንጅት መፍረስ ተጠያቂ የኾኑት ሦስቱ አካላት “የቅንጅት አመራር፣ ሲ አይ ኤ እና ወያኔ/ ኢሕአዴግ” ናቸው። ፕሮፌሰር ለቅንጅት መፍረስ ኢሕአዴግን ብቻ ተጠያቂ ማድረግ እንደማይቻል ረገጥ አድርገው አስረድተዋል። ገና ከቅንጅቱ መመስረት ጀምሮ በሁለቱ አባል ፓርቲዎች (በኢዴፓ እና መኢአድ) መካከል የነበረውን የቆየ ቁርሾ ለማስታረቅ ይደረግ የነበረውን ጥረት ዳስሰዋል። አባሪ አድርገው የመጽሐፉ አካል ባደረጉት የስንብት ደብዳቤያቸውም ውስጥ ከቅንጅት ምክር ቤት ራሳቸውን ያገለሉበት ምክንያት ይኸው የአቶ ልደቱ እና የኢንጂነር ኀይሉ ሻውል የማይፈታ ቅራኔ መኾኑን ገልጸዋል፤ ችግሩ ካልተፈታም ሊመጣ የሚችለውን ተንብየዋል።
እንደብዙ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ትዝታውን እያደነቁ በሚያስታውሱት የሚያዝያ 30 ሰልፍም ላይ የነበረውን አንድ ትዕይንት ይጠቅሳሉ። መራጩ ሕዝብ ለሰላም እና ለለውጥ ያለውን ፍላጎት እያስታወሱ በማወደስ፤ በቅንጅት አመራሮች መካከል ተፈጥሮ የነበረውን እና ለመፍረሱም ዋነኛ ምክንያት አድርገው የሚቆጥሩትን “የሥልጣን ጥም” ለማስረዳት ይሞክራሉ። “ብርሃኑ ነጋ አስቀድሞ ወደደቡብ ሄዶ ስለነበረ የሚያዝያ 30ን ሙሉ ተዓምር አላየም፤ ልደቱ አያሌው ዘግይቶ በመምጣቱ እንደሰርገኛ በመኪና ላይ ኾኖ ገባ፤ በዚያ ቀን በመስቀል አደባባይ በመኪና የመንቀሳቀስ ፍላጎቱ ከየት መነጨ?” ፕሮፌሰር በዚያ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የነበረውን ኹኔታ ከቅንጅት አመራሮች የዕለቱ ተግባር ጋር እያስተያዩ ይጠይቃሉ። በመጨረሻም ይኸው ትዕይንት ለቅንጅት እጣ ፈንታ የነበረውን ንግር ይተረጉማሉ። “የብርሃኑ አለመኖር፣ የልደቱ ለብቻው በመኪና ላይ ኾኖ እጆቹን ማውለብለብ፣ የሌሎቹ በሀይሉ ሻውል ዙሪያ መሰባሰብ የቅንጅትን የወደፊት አኪያሄድ አመላካች ነበሩ።” እነዚህም ሦስት ሰዎች በቅንጅት መፍረስ ውስጥ የነበራቸውንም ድርሻ ችግራቸው ነው ከሚሉት የሥልጣን ጥም ጋር ማስረጃ እየጠቀሱ አሳይተዋል። አቶ ልደቱ አያሌው የነበረባቸው ችግር ከሌሎቹ የተለየ እንዳልነበረም ተናግረዋል። የአቶ ልደቱን የተለየ የሚያደርገው ለቅንጅቱ መፍረስ የመጀመሪያ የኾኑ ርምጃዎችን መውሰዱ ላይ እንደነበረም አስረድተዋል። ከዚህም አልፎ አቶ ልደቱ ቅንጅትን “በምርጫ ቦርድ እና በወያኔ/ኢሕአዴግ ሊያስመቱ የሚችሉ ሐሳቦችን” ደጋግሞ መናገሩን ገልጸዋል።
“ሌላው በፕሮፌሰር መሥፍን መጽሐፍ ውስጥ የሚገለጠው ጠንካራ ተቺነታቸው ነው። ሐሳባቸውን ሲገልጹ እግረመንገዳቸውን የሚያገኙትን አግባብ ያልመሰላቸውን ነገር ሳይሸነቁጡት አያልፉም። ማኅበራዊ ኑሮውን፣የትምህርት ሥርዓቱን፣ ዩኒቨርስቲውን፣ ባለስልጣኖቹን፣ ሸምጋዮቹን፣ የፍርድቤቱን አኪያሄድ፣ መንግስትን ተቃዋሚዎችን… ትችቱም ከባድ ከመኾኑ የተነሳ ጸሐፊው ጠብ ያለሽ በዳቦ ባይ ያስመስላቸዋል። ነገር ግን የትችታቸውን ያህል በጎ ጎንን ለማድነቅ ወደኋላ አለማለታቸው ሲታይ ይህ ግምት ትክክል አለመኾኑ ግልጽ ይኾናል። ኋላ አለማለታቸው ሲታይ ይህ ግምት ትክክል አለመኾኑ ግልጽ ይኾናል። የገዢውንም ፓርቲ መልካም ነገሮች ቢኾን (ጥቂት ቢኾኑም) ያመሰግናሉ።በዚህም የመምህርነታቸው እውነተኝነት ይታይባቸዋል። ቀይ ብዕራቸው የተሳሳተውን ለመንቀፍ እና ያለማውን ለማመስገን ወደኋላ የማይል መስሎ ይታያል። ነቀፋቸውን ለመቀበል ሰሚ ጆሮ የሚያገኙ ባይመስልም። ያም ኾኖ “ይህ ስብእናቸው በሁለት ተቧድኖ ቡጢ በሚቃመሰው አንድነት ውስጥ ያለው ስፍራ ተገቢ ነወይ?” የሚለው ጥያቄ መነሳቱ አይቀርም። ለብዙዎች የፕሮፌሰር መሥፍን እንኳን በአንድነት አንጃ ውስጥ ቀርቶ በቅንጅት ውስጥ መግባታቸው አይዋጥላቸውም። ሰውየው ከዚህ ይልቃሉ ብሎ የሚያስባቸው ብዙ ነው።
ፕሮፌሰር መሥፍን በመጽሐፋቸው ውስጥ ማንንም በቋሚ ጠላትነት እንዳልፈረጁ የሚጠቁሙ ፍንጮችን አሳይተዋል። በጠነከረ ትችት ድርጊታቸውን የሚያወግዟቸውን ሰዎች ጭምር ለበጎ ጎናቸው ያላቸውን አድናቆት ሳይገልጹ አያልፉም። በአሁኑ ወቅት ሆድ እና ጀርባ መኾናቸው ከሚታወቀው ኢንጅነር ግዛቸውን ጭምር ባልዋሉበት እንዳይወቅሷቸው ጥንቃቄ ሲያደርጉ ይታያል። ያደረጓቸውን በጎ ነገሮች ጭምር በማስታወስ አድናቆታቸውን ይገልፃሉ። በምርጫው ውስጥ ታይተው ለነበሩት አስገራሚ ውጤቶች የኔ የሚሉትን አስተዋጽዖ ሲናገሩ አይታይም። በተቃራኒው ደግሞ በአሁኑ ወቅት በተጻራሪነት የሚታዩ ቢኾኑም በወቅቱ ትልቅ ድርሻ የነበራቸውን ሰዎች እያነሱ አድራጎታቸውን ማድነቃቸው አንባቢን ሊያስገርም ይችላል። “የሆነው ሆኖ ሀይሉ ሻውል፣ ብርሃኑ ነጋ እና ልደቱ አያሌው የ1997 የምርጫ ፖለቲካ እንቅስቃሴ በኢትጵዮያ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚያስገርም የጋለ መንፈስ ትጋትና ቆራጥነት የመሩት እና ያንቀሳቀሱት ሰዎች መሆናቸው ጥርጥር የለውም፤ ስኬታማ ሥራቸውን ያገዘው ያደረባቸው የሥልጣን ጥም መሆኑን ስንገነዘብ የሥልጣን ጥምን በጎ ጎን እና አስፈላጊነት እንገነዘባለን።”
በፕሮፌሰር መሥፍን መጽሐፍ ውስጥ ጸሐፊው ስለራሳቸው የነገሩን እጅግ ጥቂት መኾኑ የሚያሳዝነን በነገሩን ጥቂት ነገር ውስጥ ያገኘነውን ብዙ ቁም ነገር መቁጠር ስንጀምር ነው። በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኘው የፕሮፌሰር መሥፍን ስብእና ወደ መንፈሳዊነቱ ያዘነበለ መኾኑ ያለ ብዙ ምርምር የሚገኝ ነገር ነው። ከልጅነታቸው ጀምሮ የነበራቸውን መንታ ተጻራሪ ስብእና አሳይተው የማይፈለገውን “ጠበኝነትን” እንዴት መግራት እንደቻሉ ይገልጻሉ። ስለ ሥልጣንም ይኹን ስለ ፍቅረ ነዋይ ሽሽታቸው እና ለእውነት የመፋለም ጽናታቸው ሁሉ መንፈሳዊ ተጋድሎ እንጂ ሌላ ነገር አይመስልም።
በመጽሐፋቸው ምዕራፍ ሁለት ላይ ፕሮፌሰር “ክፉ ቀን ጥሩ ነው” በሚል ርዕስ የጻፉትን ተመስጧቸውን መጥቀስ እውነታውን ያጎላዋል። ከ97 ምርጫ ማግስት ጀምሮ በቅንጅት መሪዎች እና በሕዝቡ ላይ የነበረውን መከራ ሌላ ገጽታ ለማሳየት የጨለማውን ሌላ ገጽታ ይተነትናሉ። “ክፉ ቀን ጥሩ ነው ያስተዛዝናል፤ ክፉ ቀን ጥሩ ነው ደጋግ ሰዎችን ይቀሰቅስና የግፍን መራራነት እንዲቀንሱት አደርጋል።” ከዚህም ምዕራፍ ውጪ ያሉትን የመጽሐፉን ክፍሎች የጸሐፊውን መንፈሳዊ ስብእና ሳያስቡ ማንበብ አዳጋች ነው። ይህም ዝንባሌያቸው ከልጅነት ጀምሮ አብሯቸው የነበረ መኾኑን የሚያስገነዝበን ፍንጭ በልጅነት ታሪካቸው ውስጥ ጠቅሰዋል።
አለቃ ታምራት ትምህርት ቤት እንዳለሁ አንድ እሙን የሚባል ጓደኛ ነበረኝ፤ እርሱ እና ሁለት ሌሎች ሆነን የዚህን ዓለም ከንቱነት ስናወራ ቆየን እና እንመንን ብለን ወዲያውኑ ወስነን ቀበናን ተሳግረን ራስ ካሣ ጫካ ገባን፤አውጡን፣ ቀጋውን፣ አጋሙን ስንበላ አመሸንና ጀምበር ቆልቆል ማለት ስትጀምር አንዱ ‘እናቴ ናፈቀችኝ!’ ሲል ወዲያው ሁላችንም ‘እኔም!’ ‘እኔም!’ እያልን ቁልቁለቱን ወርደን በየኔታችን ገባን፤ስለዚህ ለአንድ ቀን ያህል መንኛለሁ!” ፕሮፌሰር ከራስ ካሣ ጫካ በጊዜ ቢወጡም አሁንም ከመናኒነት ሕይወት የወጡ አይመስሉም።
ጥሩ ግምገማ ነዉ።
ጥሩ አጻጻፍ ነው። ከበድ ያለ ጉዳይ ለአንባቢ በአጭሩ ሊጨበጥ እንዲችል ተደርጎ ቀለል ባለ መንገድ ቀርቧል። ድንቅ ችሎታ!